(ሂላሪያ ተስፋዬ እና ዕዝራ እጅጉ ተወዳጅ ሚድያ)
ፕሮፌሰር በቀለመኮንን ለተወዳጅ ሚድያ የቅርብ ወዳጅና ቤተሰብ ነው። የምንሠራውን የስነዳ ፕሮጀክት በሙሉ ልብና መንፈስ የሚደግፍ ቀና ምሁር ነው። ታናሾቹን ለማገዝ በቀዳሚነት የሚሰለፍ ኩራት ያልፈጠረበት ታላቅ ወንድም እንደማለት ነው። ከ4 ዓመት አስቀድም “መዝገበ አእምሮ” ቅጽ አንድ ሲዘጋጅ ከጀርባ እና ከጎን ሆኖ ሲረዳን ነበር። የኃይሉ ልመንህን ታሪክ ፕሮፌሰር በቀለ አስታውሶ ታሪኩን ባይነግረን ኖሮ ኃይሉ ልመንህን አናገኘውም። ፕሮፌሰር በቀለ ሌሎችም ስሙን ከአክብሮት ጋር የሚያነሱት የሥነጥበብ ሰው ነው።
ተወዳጅ ሚድያ እስከዛሬ የ432 ባለሙያዎችን ታሪክ በመፅሐፍ፣ በዲጂታል ሚድያ እና በድምፅ ሲሰንድ ፕሮፌሰር በቀለ መኮንንም እንዲካተት አድርጓል። እስከዛሬ በሚዲያ እና ኪነ-ጥበብ ዘርፍ የሠሩትን በምንችለው አቅም ታሪካቸው ዘመን እንዲሻገር ያደረግን ሲሆን የስነዳ ተግባሩም ተጠናክሮ ቀጥሏል። በቀጣይ እያዘጋጀነው ባለነው ዕትም ከ20 ዘርፎች የተውጣጡ ታላላቆችን በማሰባሰብ ላይ እንገኛለን ። ከእነዚህ ታላላቆች ውስጥ ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን አንዱ ነው። የሕይወት ታሪኩንም ብዙ ካልታዩ የልጅነት ምስሎቹ ጋር አንድ ላይ በማድረግ ታሪኩን አጋርቶናል። ዕዝራ እጅጉ እና ሂላሪያ ተስፋዬም ታሪኩን እንደሚከተለው ሰንደውታል።በነገራችን ላይ በዚህ የሕይወት ታሪክ መጣጥፍ ውስጥ ተባባሪ ፕሮፌሰር ቴዎድርስ ገብሬ “በቀለን በብሔራዊ ትእምርት ፍለጋ ውስጥ” ብሎ የጻፈው ረዘም ያለ ምሁራዊ ትንተና አቅርበናል። የፕሮፌሰር በቀለ መምህር ወርቁ ጎሹ የሰጡትንም ምስክርነት አካተናል። መልካም ንባብ።
የሰባተኛ ክፍል ተማሪ እያለ የስዕል ዝንባሌውን እንዲከተል እንዲሁም የስዕል ትምህርትን እንዲማር ያመለከቱትን መምህሩን በአንደበቱ ቃላት ይስላቸዋል። እኚህ መምህሩን፥ “ሊከተሉት የሚገባ ሰው” ሲል ይገልጻቸዋል። ምንአልባት ከበርካታ ዓመታት በኋላ እርሱ ራሱም እንዲያ ያለ ‘ሊከተሉት የሚገባ’ የጥበብ ሰው ሊሆን እንደሚችል አልገመተ ይሆናል።
ፍላጎቱ ከእኩዮቹ የተለየ፣ ‘ተርታ’ ለሆነ ነገር መሻት የሌለው፣ በለጋ እድሜው ሳይቀር ነገሮችን እንደሆኑ ማየትና መሥራትን የማይመርጥ፣ አዲስ ነገር መፍጠርን አልያም የነበረውን በአዲስ መልክ መቃኘት ይቀናው የነበረ ተማሪ ነው። ስሙን ሳይቀር በስዕል ይጽፍ እንደነበር ይናገራል። በስጋው ላይ ያሠለጠናት ነፍሱ፥ ሰዓሊ የመሆን ግቡን ለማሳካት ይችል ዘንድ ‘የሰው ልጅ መሠረታዊ ነገሮችን’ አሻግሮ እንዲያይ ጉልበት ሰጥታዋለች። ይህ ጉልበትና ጽናት ነው፣ አሁን በሥነ ጥበብ ዘርፍ በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን ሙሉ ፕሮፌሰር የወለደው፥ ሠዓሊና ቀራፂ ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን።
ትውልድና እድገቱ ደብረዘይት (ቢሾፍቱ) ከተማ ነው። ጥር 6 1956 ዓ.ም። ትምህርትን አሃዱ ያለው በቆሎ ትምህርት አቡጊዳ ብሎ ፊደል ቆጥሮ፣ ዳዊት ደግሞ ነው። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን አፄ ልብነ-ድንግል ወናግሰገድ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፣ እንዲሁም ኹለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በዚያው ደብረዘይት ልዕልት ተናኘወርቅ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትሏል። የ12ኛ ክፍል ማጠቃለያ ፈተናውን የወሰደው ደግሞ በአዲስ አበባ ምኒልክ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው።
ከልጅነት እድሜው ጀምሮ የተገዛው ለስዕል ጥበብ ብቻ ሳይሆን በጠቅላላ ለጥበብ ነበር። አዲስ ነገርን አልያም የነበረው በተሻለ መንገድ ሆኖ ማየትን ይመርጣል። በጥበብ ለሚሠራ ነገር ሁሉ ልዩ ፍቅር አለው። አሁን በአዋቂነትና በርቱዕ አንደበቱ ውበት እንደሚገዛው፥ ሰው የማይሠራውን መሥራት አልያም የተሠራውን ነገር ባልተሠራበት መንገድ መሥራት እንደሚወድድ ይናገራል። ይህን ቃሉን በልጅነት እድሜው ሲገልጥ ደግሞ፣ ስሙን ሳይቀር በስዕል ይጽፍ ነበር።
የተካነበት፣ የሠለጠነበትና የታወቀበት የስዕል እና የቅርጻ ቅርጽ ጥበብ ይሁን እንጂ፥ ለጽሑፍ ጥበብ እና ውበትም ስሱ ነው። በልጅነትና ወጣትነት እድሜው በደብረዘይት ኪነት ውስጥ ቴአትር፣ ግጥም እንዲሁም መፈክር ጭምር በመጻፍ ይታወቃል። እንደውም ለተማሪዎች፣ ለሰፈሩ ወጣቶች የጻፋቸው የፍቅር ብሎም ልዩ ልዩ ደብዳቤዎችና ግጥሞች ጋር በተያያዘ በተለያየ አጋጣሚ የሚያነሳቸው ገጠመኞቹ ጥቂት አይደሉም። የእጅ ጽሑፉን ብቻ ሳይሆን የሚጽፋቸው ጽሑፎችና ግጥሞች ይዘት ጭምር ነበር ብዙዎችን የሚስበው።
በኋላ 12ኛ ክፍል ፈተናን ከመውሰዱ አስቀድሞ፥ የስዕል ትምህርትን ለመማርና መምህሩ የዘራበትን ዘር ለማፍራት ዝንባሌውን ተከትሎ በዘመኑ አዲስ አበባ የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤት (አሁን አለ ሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት) አቀና። ትምህርት ቤቱን ለመቀላቀል ደጅ ጥናትና ምልልስ እንዲሁም ተማጽኖ አስፈልጎታል። በኋላም ተሳክቶለት ተማሪ ለመሆን በሚጠበቀው ፈተና አንድ ሺህ ከሚጠጉ ተወዳዳሪዎች መካከል ከ14 አላፊ ተማሪዎች አንዱ መሆን ቻለ።በ1971።
በአንድ ወቅት በአራዳ ኤፍኤም አዲስ አራዳ የራድዮ ፕሮግራም ላይ ባደረገው ቆይታ፣ የዚያን የአምስት ዓመት የትምህርት ዘመን ሲያነሳ፥ በትምህርት ቤቱ የነበረው የ5 ዓመት ቆይታ ቀላል እንዳልነበር ያስታውሳል። ሌሊት ማረፊያ የሚያጣባቸው ቀናት ብዙ ናቸው። ምንም እንኳ ለአምስት ዓመታት እያንዳንዱ ቀን የአንድ ዓመት ያህል ከባድ የነበር ቢሆንም፥ እርሱ ግን ‘ቀኑን ጎበዝ መሆን ነበር የሚፈልገው’። እናም ቀኑን ጎብዞ ከባዱን ጊዜ በብልሃትና በጽናት ተወጣው። ትምህርቱን አጠናቅቆም በማዕረግ ተመረቀና እዚያው የተማረበት ትምህርት ቤት መምህር ሆኖ ተቀጠረ።
በተማረበት ትምህርት ቤት በወጣት መምህርነት ለአራት ዓመታት አገልግሏል። ከዚያ በኋላ፥ ወደ ሩሲያ ለከፍተኛ ትምህርት ተላከና ሞስኮ ከተመ። ‘ግራጫ’ ይለዋል፣ የሩስያን ፀሐይ አልባ ቀዝቃዛና ደመናማ የጨላለመ የዘመኑን ድባብ። በዙሪያው ውበትን ማሰስ የለመደ ዐይኑ በሞስኮ ያንን ሊያገኝ አልቻለም። እንዲያም ሆኖ የደከመለት ትምህርቱን ለመፈጸም ጽናትን በመምረጥ፥ ከስድስት ዓመት የሞስኮ ቆይታ በኋላ የከፍተኛ የሥነጥበብ ትምህርቱን በሚገባ አጠናቅቆ ወደ እናት ሀገሩ ኢትዮጵያ ተመለሰ።
ከሩስያ መልስ አስቀድሞ በመምህርነት ያገለግልበት በነበረው ሥነ -ጥበብ ትምህርት ቤት የማስተማር እድል አገኘ። በዚያም በመጀመሪያ በሥነ ጥበብ ታሪክ ከዚያም በንድፍ ጥናት መምህር ሆኖ ቆይቷል። በመምህርነት ብቻም አይደለ፥ በጊዜው ‘አርት ስኩል’ ይባል የነበረውን ይህን ትምህርት ቤት፣ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋምነት ለማሳደግ ከ1990ዎቹ ጀምሮ ለዓመታት በዘለቀውና በተደረገው እልህ አስጨራሽ ትግል ውስጥ ከፊት ሆነው ሲያስተባብሩ ከነበሩት መካከል ሆኗል። በመጨረሻም ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ በተሰጠ የጥናት ውሳኔ ሥነ ጥበብ ትምህርት ቤቱ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተዛውሮ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ሲሆን ትልቁን ድርሻ ከተወጡት ጥቂት ግለሰቦች መካከል ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን ተጠቃሽ ነው።
ትምህርት ቤቱ የዩኒቨርሲቲው አንድ አካል ክፍል ከሆነ በኋላ የመጀመሪያው ዳይሬክተር በመሆን ሠርቷል። በዚያም ወቅት የትምህርት ቤቱን ነባር ስርዓት የከፍተኛ ትምህርት ስርአት ቅርፅ ለማስያዝ በብርቱ ለፍቷል፣ አሳክቷልም። በ2009 ዓ.ም ገደማ የሥነጥበባት ኮሌጅ ሲመሠረት በድጋሚ የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር ሆኖ ከማገልገሉ ባሻገር፥ ትምህርት ቤቱ መጠሪያው ወደ አለ የሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት የተቀየረው የኮሌጁ ዲን ሆኖ ባገለገለበት ዘመን ነበር። ከዚያም ባሻገር አዲስና ተጨማሪ የፊልም ትምህርት ክፍል እንዲቋቋም ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ትምህርት ክፍሉ እውን እንዲሆን አስችሏል። ከዚህም ባሻገር በማስተማርና በማማከር በርካታ ተማሪዎችን ያፈራ ብርቱ ባለሙያ ነው።
ፕሮፌሰር በቀለ በብሉይ ወይም ክላሲክ አካዳሚ ትምህርቱን ጠንቅቆ የተማረ ይሁን እንጂ በዘመነኛ የሥነ ጥበብ እንቅስቃሴ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ከሚጠቀሱ ባለሙያዎች አንዱ ነው። አዳዲስ ሙከራዎችና አሰሳዎችን በድፍረት ግን በኃላፊነት በማከናወን ሁሌም ፈር ቀዳጅና አዲስ መንገድ የሚያሳይ ከልቡ የፈጠራ ሰው ስለመሆኑም ብዙዎች ይመሰክራሉ፥ ከዚያም በላይ ሥራዎቹ ምስክሮቹ ናቸው።
ፕሮፌሰር በቀለ የመጀመሪያ የሥዕል ኤግዚቢሽኑን ያቀረበው ከሀገር ውጭ ፊንላንድ፥ ‘ኮ’ፕዮ’ የሚባል ዩኒቨርሲቲ (Kuopio – በአሁኑ ምሥራቅ ፊንላንድ ዩኒቨርሲቲ) ነበር። ይህም በሞስኮ የሥነጥበባት የመጨረሻ ዓመት ተማሪ እያለ ሲሆን፣ ለዕይታ ያቀረባቸው ሥራዎቹም የተለያዩ አስቀድሞ በትምህርት ቤት ቆይታው ያዘጋጃቸው ናቸው።
ከዚያ በኋላ ለቁጥር በርካታ፣ ለዓይነት ብዙ፣ ለዐይን ውብና አስደማሚ የሆኑ ሥራዎችን ያለማቋረጠ ለበርካታ ዓመታት ሲያቀርብ ቆይቷል። ከስዕል ኤግዚቢሽን እስከ አደባባይ ሐውልቶችና ዓለም አቀፍ መድረኮች፥ በቀለ መኮንን የሚለው ስም እንግዳ ሆኖ አያውቅም።
በ1996 ዓ.ም ያቀረበው ‘እንቆቅልሽ’ የተሰኘ የ‘ኢንስታሌሽን ጥበብ’ ትርዒቱ ዘይቤያዊ (Methaphorical) ትርጉም የያዘና አሁንም ድረስ አነጋጋሪ ሆኖ የቆየ ሥራ አንዱ ተጠቃሽ ነው። በ2000 ዓ.ም ‘እድልና ምርጫ’ የሚል ‘ክሪቲካል’ ትርዒቱን አቅርቦ ተመልካቹን አስደምሟል። በ2010 ዓ.ም ‘ባሩድና ብርጉድ’ ሲል የሰየመው አነጋጋሪና አወያይ ኤግዚቢሽኑ፥ ተመልካቹ ስለ ሥነጥበብ ያለውን አመለካከት ደጋግሞ እንዲፈትሽ ያስገደደ ነበር።
በ2016 ዓ.ም በኢትዮጵያውያን የሕይወት ዘይቤ ላይ ትልቅ ጥያቄ አንስቶ ያወያየውንና እስከ አሁንም የሚያወያየውን “ግሉተን ፍሪ-ደም” ወይም ‘ጤፍና ነፃነት’ የተሰኘውን ልዩ ትርዒት አቅርቦ የሥነ ጥበብ ተመልካቾችን ማስደነቁና ማነጋገሩን ቀጠለበት።
ከ25 ዓመታት በላይ እነዚህን የፈጠራ ሥራዎቹን በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር በተለያዩ መድረኮች ሲያሳይ ቆይቷል። በአፍሪካ፣ በአውሮፓ እና በአሜሪካ፣ በተለያዩ ሙዚየሞች ሥራዎቹን አቅርቧል፣ ሐሳብና ዕይታውን አስደምጧል። ሀገሩን አልፎም አኅጉሩን አፍሪካን በዓለም መድረክ በዘርፉ በኩራት እንዲቆሙም ምክንያት ሆኗል።
በቅርብ ማለትም ባለፈው 2017 ዓ.ም፥ በኢጣሊያ ቱሪን ከተማ ሮያል ፓላስ ሙዚየም ተጋብዞ ‘ዘ ስሞኪንግ ቴብል’ ወይም ‘የሚጤሰው ጠረጴዛ’ የተሰኘ ፀረ ቅኝ ግዛት ይዘት ያለው ዘመነኛ የሥነ ጥበብ ሥራ በመፍጠር ለዕይታ አቅርቧል። ይህም ከፍተኛ እድናቆትን ያስገኘለት ብሎም ሐሳቡን ያስደመጠበት አውድ መሆን ችሏል።
መሥራት እንጂ ይህን ሠራሁ ብሎ መናገርን የማያዘወትረው ፕሮፌሰር በቀለ፣ እንዲህ ካሉ አውደ ርዕዮች ባሻገር በቀራጺነቱ የተጠበበባቸው ሥራዎችም እጅግ በርካታ ናቸው። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሠራቸውን በማማከር የተሳተፈባቸውን ብቻ ለመጥቀስ፥ በሙሉ ነሃስ የተሠራው የቀዳማይ ኃይለሥላሴ ኪነ ሀውልትን ጨምሮ፥ አብርኆት የሕዝብ ቤተመጻሕፍት ደጃፍ የሚገኘው ኪነ ሀውልት (ከነሐስ ቀልጦ የተሠራው ሕፃን)፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዋና መሥሪያ ቤት ያሠራው ሕንጻ ጋር የሚገኘው የባንኩን ዓላማና ርዕይ የሚያሳየው ግዙፍ ኪነ ሀውልት (ሀብት ካለ በሰማይ መንገድ አለ) እጅግ ጥቂቶቹ ናቸው።
ታድያ ለእነዚህና ለበርካታ ሥራዎቹ ሽልማቶችና እውቅናዎች ተበርክተዉለታል። ከእነዚያም መካከል በ1990 ዓ.ም የቺካጎ አርቲስቶች ዓለም አቀፍ ሽልማትን ያሸነፈ ብቸኛው አፍሪካዊ የስነ ጥበብ ባለሙያ መሆን ችሏል። እ.ኤ.አ. በ2006 በአሜሪካ ኒው-ዮርክ ውስጥ የIIE ፕሮግራም የሆነውን የ’Scholar Rescue Fund’ ሲቀበል የመጀመሪያው የሥነ ጥበብ ሰው ነበር። በዚያው ዓመት በባልቲሞር ሜሪላንድ ውስጥ በተጋባዥ ሠዓሊነት በበሜሪላንድ የአርት ኮሌጅ (MICA-Maryland institute college of Art) ለስምንት ወራት ቆይታ አድርጓል።
ፕሮፌሰር በቀለ የኢትዮጵያ ሚሌኒየም ዓርማ ነዳፊ ሲሆን በመላ ሀገሪቱ በርካታ ኪነ ሀውልቶችን ነድፏል፣ አቅዷል፣ አማክሯል፣ መርቷል፣ ሠርቷል። በርካታ የመጻሕፍት ሽፋኖችንና የውስጥ ምስሎችን አዘጋጅቷል። በሀገር እና በዓለም አቀፍ የሥነጥበብ እና የሥነ ሕንፃ የውድድር መድረኮች ላይ በከፍተኛ ዳኝነት አገልግሏል።\ ከስነጥበቡ ማኅበረሰብ ውስጥ ደግሞ በኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ መደበኛ አባል ነው።
ከዚህም በላይ ከእለት እለት የማስተማር ተግባሩ ጎን ለጎን በቅርቡ በተባበሩት መንግሥታት ፕሮጀክት ስር ነባሩ የአፍሪካ አዳራሽና የሥነ ጥበብ ሥራዎቹ እድሳት ውስጥ ባለሞያ፣ አማካሪና ተቆጣጣሪ በመሆን የተሳካ ሙያዊ ተልዕኮ ፈፅሟል። በአሁኑ ወቅትም በአለ ሥነጥበብ እና ዲዛይን ትምህርት ቤት የቅድመ እና ድኅረ ምረቃ ፕሮግራም ፕሮፌሰር ሲሆን፣ የዘመናዊ ሥነጥበብ ሙዚየም ገብረ ክርስቶስ ማዕከልንም በመምራት ላይ ይገኛል።
ኅዳር 4 ቀን 2018 ዓ.ም የአለ የሥነጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት የቀድሞ ተማሪዎች በትምህርት ቤቱ የአክብሮትና የምስጋና ፕሮግራም አድርገዉለታል። ተማሪዎቹ ያንን ያደረጉት ፕሮፌሰር በቀለ በጀርመን ሀገር ፍራንክፈርት ከተማ ከሚገኝው የሥነጥበብ ዩንቨርሲቲ ጋር ከዓመታት በፊት የተጀመረውን የኹለትዮሽ ግንኙነት ዳር በማድረስ ላደረገው ታላቅ ተግባር እና የትምህርት ቤቱን ዳግም ትንሳኤ ለማሳካት ድልድይ በመሆኑ በማመስገን ነው።
አሁን ታድያ ይህና ያልተነገረ እጅግ በርካታ፣ ውብና አስደናቂ፣ ገና ያልተተነተነና ዐይን የሚሻ ሥራን የሠራ ሰው ነው፥ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የሥነጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት የመጀመርያው ሙሉ ፕሮፌሰር ማዕረግ የተሰጠው።
#ምንአሉ?
ይህንን ዜና በደስታ በማኅበራዊ ገጾቻቸው ካጋሪት መካከል ጋዜጠኛ #ቴዎድሮስተክለአረጋይ እንዲህ አለ፥
“አንዳንድ ጊዜ ማዕረግም፣ ሹመትም፣ ሽልማትም በተለያዩ ምክንያትና አጋጣሚዎች ያልተገባ ሰው እጅ ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ። ይህ ይበልጡን በሀገራችን፣ በዓለምም ላይ ታይቷል። ለፕሮፌሰር በቀለ መኮንን ዓይነቱ ደግሞ እንዲህ ግጥም ያለ ፣ በልኩ የተሰፋ ይሆናል። የበቄ ፕሮፌሰርነት በሥነ ጥበብ ዘርፍ የተሰጠ የመጀመሪያው ቢሆንም የሰውየው የበቀለ ብቻ አይደለም። የመጭው ትውልድ ሁሉ ነው። የሥነ ጥበብነት ብቻ ሳይሆን የመቻል ፕሮፌሰርነት ነው። ከእንግዲህ ለአንድ ጥበበኛ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ መሰጠት እንደሚችል ማሳያው፣ ማመላከቻው፣ ዳገቱ፣ ምልክቱ ነው፥ በቀለ መኮንን። ያሉትና የመጭዎቹ የሥነጥበብ ልሂቃን ተስፋና ብርታት ነው። እንደሚቻል ማሳያውም፣ ማረጋገጫውም ሆኗል። ይህ ለሥነጥበቡ ብቻም ሳይሆን ለሙዚቃውም ፣ ለትያትሩም ነው።”
የሙያ አጋሩንናበአለ የሥነ ጥበብ እና ዲዛይን ትምህርት ቤት ዲን #ሠዓሊአገኘሁአዳነ በበኩሉ፥ “የቤት ሰው፣ መምህር፣ ባልደረባ፣ የሞያ አባት… ከፍ ሲል፣ ሲከብር፣ ድካሙ ፍሬ ሲያፈራ ወዘተ. ልብ ይሞላል። በቀለ መኮንን ንጉሡ ባለግዙፍ ሰብዕና፣ ከሰው ፊት የሚያቀረቡት፣ የሚያኮራ፣ ጥንቅቅ ያለ ሙያተኛ፣ በጥረቱ ከጉልበተኞች ቅሚያና ንጥቂያ፣ ከሰሜነኛው ንፍቀ ክበብ (global north) በር ጠባቂነት በጥበብ ሾልኮ በርካታ ዓለማቀፍ መድረኮችን የተጋራ፣ ረብ ያለው ተግባር እየፈጸመ ያለ ሰው የሚሠራበት ተቋም አዲስ አበባ ዮኒቨርስቲ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ሰጥቶታል። የአለ የሥነጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት የመጀመርያው ሙሉ ፕሮፌሰርሽፕ ማዕረግ መሆኑ ነው።” ሲል አያይዞ የእንኳን ደስ አለህ መልዕክቱን እስተላልፏል።
ደራሲእንዳለጌታከበደ (ፒኤችዲ) “አሁን የሆንከውን ለመሆን፣ አንተው ራስህ የጻፍከውን ግጥም ኖሮ መገኘትን ይጠይቃል።” ሲል መግቢያ አኑሮ ባጋራውና ራሱ ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን በጻፈው ‘ቼ በለው’ በተሰኘው ግጥም እናብቃ፥
ቼ በለው!
ሕይወት ጎዳናው ገጹ ሲለወጥ
በጭነት ታክቶ ጀርባው ሲመለጥ
የእንቅፋት አጽሙ ቋጥኙ ሲገጥ
ሸክም ዘንቦበት ትቢያው ሲላቆጥ
ሲሆን ድጥ በድጥ
ሾህ ጭቃ ቅይጥ
ልብህ አይደንግጥ።
በምኞት ቅዥት በስጋት ርዶ
አይፍረስ ግንቡ ወኔህ ተንዶ
ከቆመው ቆመህ ከንፈር ከመምጠጥ
በተስፋ ፈረስ በልጓም ሸምጥጥ።
አያረጅ የለም አይለዋወጥ
ነገን ተማምነህ በመጓዝ ቁረጥ…
ከሩቅ አልመህ ቅርብ አትርመጥመጥ
ሰግተህ ከምትቆም ስትጋልብ ፍረጥ።
#መምህሩጋሽወርቁ ስለ ፕሮፌሰር በቀለ
መምህር ወርቁ ጎሹ የፕሮፌሰር በቀለ መኮንን አስተማሪ ሲሆኑ የ85 ዓመት ሰውም ናቸው። በቀለ ከወጣትነቱ አንስቶ ህልሙን ለማሳካት ታላቅ ጥረት የሚያደርግ ተማሪዬ ነው ሲሉ በኩራት ምስክርነት ይሰጣሉ። መምህር ወርቁ ጎሹ ቀራጺ በቀለ ከሰዎች ጋር የመግባባት ክህሎትን የታደለ የሚወደውን ሙያ እየሠራ ያለ ብቃት ያለው የሥነ ጥበብ ባለሙያ ነው ሲሉ ይገልጹታል።
ጋሽ ወርቁ 30 ዓመታት አስተምረዋል። በቀለን ሲገልጹት የሚደነቅና የሚከበር ይሉታል። በራሳቸው ጥረት ካደጉት ተርታ ይመድቡታል።
ጋሽ ወርቁ ወደ ኃላ መለስ ብለው የፕሮፌሰር በቀለን የትምህርት አቀባበል ሲያጤኑ የቀን የሌት ጥረት የሚያደርግና የልፋቱን ያገኘ በሚል ያስረዳሉ። ተሰጥዖም የሚታይ ነው ይላሉ።
ዛሬ ፕሮፌሰር መሆኑ ለአገር ትልቅ ኩራት መሆኑንም ነግረውናል።
” የበቀለ ፕሮፌሰር መሆን ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለአገር ኩራት ነው። እኔ እንደ አስተማሪው ይህን የምሥራች ስሰማ ደስታዬ ያይላል።እንኳን ደስ ያለህ ልለውም እወዳለሁ። “ሲሉ ለተወዳጅ ሚድያ ምስክርነት ሰጥተዋል።
በቀለ መኮንን፤
በብሔራዊ ትእምርት ፍለጋ ውስጥ
#በተባባሪፕሮፌሰርቴዎድሮስገብሬ
I
ከብረት እስከ ጨርቅ በደረሱ ትይዩ ተቃራኒዎች መካከል ሲያመላልሰን የከረመው በቀለ መኮንን፣ ጥቁር ጤፍ ፈጭቶ–ጥቁር ጤፍ አቡክቶ “በጋገራቸው” ኪነቶች አማካይነት ሊፈትነን “ጤፍና ነጻነት” የሚል ርእስ በሰጠው አዲስ ትርኢት ተገልጧል፡፡ “ጤፍ” እና “ነጻነት”? ጤፍ ገቢር ነው፡፡ ነጻነት ደግሞ ኀልዮ፡፡ ጤፍ ይሰፈራል፤ ይፈጫል፤ ይቦካል፤ ይጋገራል፡፡ ነጻነት ግን በኅሊና ይነደፋል፡፡ ጤፍ እና ነጻነት በነገረ ፍጥረታቸው አይገናኙም፡፡ ‘እናስ በምን ተጠየቅ ተዛምደው በአንድ ርእስ ውስጥ በ“እና” ተዳሩ?’ የሚል ጠያቂ ከመጣ ምላሹን የሚያገኘው ከትርኢቱ ዐውድ ይሆናል፡፡
በቀለ በትርኢት መግለጫዎቹ በገሀድ እንደሚጠቁመን በአዳዲስ ሥራዎቹ ውስጥ ረቂቁ “ነጻነት” በግዙፉ ጋሻ ውስጥ አድሮ ተጨባጭ ሆኗል፡፡ በእርግጥ ጋሻ የሚመስሉ “እብጠቶች” በበቀለ ዕይታዊ መድበለ ቃላት ውስጥ የሰርክ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በቀደሙት ትርኢቶች ውስጥ ጋሻዎች አንድም ቅርጽ ከቅርጽ ተጋጭተው ለሚፈጥሩት “ግብታዊ” ፍቺ ሲባል ይመላለሳሉ፤ አንድም ደግሞ የማረሻን የገነነ ወንዴነት ማስከኛ ሆነው በሚዛን ጠባቂነት (as a feminine energy) ይመጣሉ፡፡ በ“ጤፍና ነጻነት” ነጻነት በጋሻ ውስጥ በማደሩ፣ ጋሻ ከቀደመ ግብሩ የተለየ አዲስና ቋሚ ሚናና ግብር ይዟል ማለት እንችላለን፡፡ አዲስ ግብር ለመያዙ ምስክሩ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በትርኢቱ ውስጥ የሚገጥሙን ጋሻዎች በሙሉ በጤፍ ዱቄት የተገነቡ (የተለሰኑ) ናቸው፡፡ የጋሻዎቹ በጤፍ ዱቄት መገንባት አንድም፣ በትእምርቶቹ መካከል የባሕርይ መጋራት እንዲፈጠር፤ አንድም በኪነቱ ውስጥ ጥንድ ምናብ–ድርብ አስተማስሎ (double representation) እንዲከሰት ዕድል ሰጥቷል፡፡ የጉዳዮች በአንድ ወደተሸረቡ መንታ ትእምርትነት ማደግ ተመልካች ሐሳቡን የሚያሰላበትን፣ ትችቱን የሚያፍታታበትን ምቹ የመፈከሪያ ዐውድ እንዲያገኝ አስችሎታል፡፡
ጋሻ የነጻነት እና የአርበኝነት ማኅደር ነው፡፡ (ይህ ዓይነቱ የጋሻ ፍቺ በተገኘበት ባህል ውስጥ ጭምር ይታወቃል፡፡) ቆየት አድርጌ በስፋት እንደማሳየው ጤፍ በፈንታው የ“ኢትዮጵያ” እና “የኢትዮጵያዊነት” ብሔራዊ ትእምርት ነው፡፡ በዚህ ዐውድ የብሔራዊ ትእምርት ፋይዳ አንድም፣ በነጻነት፣ በአገር እና በብሔራዊ ምንትነት መካከል ያለውን ረቂት ተራክቦና ውስብስብ ተጻምሮ ተጨባጭ ማድረግ ነው፡፡ አንድም ደግሞ ተራክቦውን–ተጻምሮውን ጠብቆ ለማኖር ዜጎች በአርበኝነት መንፈስ የሚከፍሉትን የላብና የደም መስዋዕትነት ማመልከት ነው ማለት እንችላለን፡፡ (በ“Gluten-free-dom II” እንጀራ የጠመጠመ ጋሻ በአናታቸው የደፉ፣ በትኩስ የአመድ ደለል ላይ/ውስጥ የቆሙ ሰባት እናቶች እንዲህ ላለው አንድምታ አስረጂዎች ይሆኑናል፡፡)
II
ብሔራዊ ትእምርቶች የብሔራዊ ምንትነት ግላጼዎች (identity expressions) ናቸው፡፡ የምንትነቱ ሥሪት (identity construction) በተረኮቹና በትእምርቶቹ ጥራትና ጥንካሬ ላይ ይወሰናል፡፡ ግላጼዎቹ እና ሥሪቱ የሚተጋገዙ ብቻ ሳይሆን የሚተካኩ ጉዳዮች ጭምር ናቸው፡፡ ያንዱ መድከም ሌላውን ያጎድላል፡፡ ያንዱ መዛል ሌላውን ያፈርሳል፡፡ የብሔራዊ ትእምርት ቀረጻ ብሔራዊ-ጥበባዊ ተልእኮ ነው፡፡ የአንድ ሕዝብ ብሔራዊ ምንትነት በአንጻራዊነት ለዘመናት ጸንቶ ይዘልቅ ዘንድ ተረኮች (ቃላዊ፣ ዕይታዊ፣ ትውናዊ፣ ወዘተ. ተረኮች) እና ትእምርቶች በጥንቃቄ መመረጥና መቀናበር፣ በየጊዜው እየተመረመሩ መታረምና መከለስ ይኖርባቸዋል፡፡ ብሔራዊ ምንትነት በዐቢይነት የውክልና ጉዳይ ነው፡፡ በአንድ አገር ውስጥ እያሉ እንደሌሉ የተቆጠሩ ወገኖች፣ ቸል የተባሉ ሰብአዊ ዕሤቶች፤ አቅም ባገኙ፣ የኃይል ሚዛን በለወጡ ጊዜ በነባር ተረኮች እና ትእምርቶች የተሸመነውን ብሔራዊ ምንትነት እስከ መሻር፣ አፍርሶ እንደ አዲስ እስከመሥራት የሚያደርስ ጥያቄ ያነሳሉ፡፡ ይህ ሲከሰት የአገር ግንባታ ሂደት ይስተጓጎላል፤ ማኅበራዊ ውጥረት ይነግሣል፡፡ (የዛሬዋ ኢትዮጵያ ለዚህ ዓይነቱ እውነታ አብነታችን ናት፡፡) በመሆኑም ብሔራዊ ትእምርት ቢያንስ ቢያንስ ረጅም የታሪክ ዘመንን፣ ሰፊ መልክአ ምድርን እና ገሀድ የወጡ የማኅበረሰብ ክፍሎችን እና ዕሤቶችን ሊያካልል ይገባል፡፡ ብሔራዊ ትእምርት ከውክልናው ፈርጀ ብዙነት ባሻገር በኪነት ከፍታው እና በኀልዮ ጥራቱም ተለይቶ መታወቅ አለበት፡፡ ጥቅል በሆነ አነጋገር፣ ብሔራዊ ትእምርት ጥልቅ በሆነ ጊዜ ውስጥ፣ ጽኑእ በሆነ መሠረት ላይ የሚታነጽ በነባርና በአዳዲስ ዕሤቶች ትብብር የሚሸመን ዐውራ ምስል ነው፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ላለ ኅብረ ባህላዊ አገር ብሔራዊ ትእምርት በትግግዝ የሚፈጸም ብሔራዊ–ኪናዊ ተልእኮ ነው፡፡ ብሔራዊ ትእምርት እርስ በርስ ሊናበቡና ሊከታተሉ በሚችሉ በግለሰብ፣ በቡድን፣ በትውልድ በሚፈጠሩ ገባር ምናቦች ትግግዝ በዘመናት ሂደት ምልዓት ላይ የሚደርስ ዐውራ ትእምርት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ኪናዊ ትግግዝ–የምናብ ተናባቢነትና የምስል ተከታታይነት–በተጨባጭ ለማሳየት “ጤፍና ነጻነት”ን በሁለት መንገዶች ማንጸር እንችላለን፡፡ ቀዳሚው መንገድ ይህንን ትርኢት ከበቀለ መኮንን ነባር ትርኢቶች ጋራ እያመሳከሩ መፈከር ሲሆን፤ ተከታዩ ደግሞ በየትኛውም የኪነት ዘርፍ ካሉ ዘመነኞቹ ጋራ–ለምሳሌ ከአዳም ረታ ጋራ–እያናበቡ ማስተሳሰር ነው፡፡ የበቀለ መኮንንን ዕይታዊ ጥበብ ከአዳም ረታ ቃላዊ ኪነት አናብቦ በብሔራዊ ትእምርትነት ለማስላት በቂ ምክንያቶች አሉ፡፡ ለዛሬው ትርኢት የነፍስ ያህል የሆነውን ዐውራ መባያ[1]–ጤፍን በበቀለ የአከያየን ልማድ ውስጥ ከገነነው፣ ከማረሻ ጋራ አስተሳስሮ ለማሰብም እንዲሁ፡፡ ከምክንያቶቹ ውስጥ መሠረታዊዎቹ፡- አንደኛ፣ የዐውድ ተዛማጅነት፤ ሁለተኛ፣ የኀልዮ (የጭብጥ) ተከታታይነት፤ ሦስተኛ፣ የቅኝት ወይንም (የርእዮተ ዓለም) ተወራራሽነት፤ አራተኛ፣ የጊዜ ጥልቀት (የነገረ ፍጥረት ብሉይነት)፤ አምስተኛ፣ ሥነ ልሳናዊ ተዛማችነት ናቸው፡፡
“ማረሻ” የግብርና ማምረቻ መሣሪያ፣ “ጤፍ” ደግሞ የግብርና ምርት በመሆናቸው በተፈጥሮ የቅደም-ተከተል ዝምድና አላቸው፡፡ (ተፈጥሯዊው ቅደም ተከተል በጉዳዮቹ መካከል አለ ያልነውን የጭብጥ ተከታታይነት እና የትእምርት ተጋጋዥነት ተጨባጭ ያደርግልናል፡፡) የማምረቻ መሣሪያው (ማረሻ)፣ የአምራቹ (ገበሬ) እና የምርቱ (ጤፍ) ተፈጥሯዊ የተራክቦ ዐውድ ገጠር ነው፡፡ ጤፍ እና ማረሻ ከ85 ከመቶ በላይ ኢትዮጵያዊ ይኖርበታል የሚባለውን፤ ዳሩ ግን በአገሪቱ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ እና ምጣኔ ሀብታዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ተገቢ ሥፍራ የተነፈገውን ወገን በቀጥታ ይመለከታሉ፡፡ ከያኒው ለተገፉ፣ ሥፍራ ለተነፈጉ ብሔራዊ ጉዳዮች ማድላቱ የትእምርቶቹን ምርጫ ተገቢነት ከማረጋገጡ ባሻገር ቅኝቱን ርእዮተ ዓለማዊ ያደርገዋል፤ (“history from below” እንደሚባለው)፡፡ ገጠርን አትኩሮ፣ ነባር የግብርና መሣሪያንና ጥንታዊ ምርትን (ማረሻንና ጤፍን) ከዚያው ዐውድ መልምሎ በምናብ ማጥለቁ፣ በምስል ማበልጸጉ እና በኀልዮ ማራቀቁ ብዙኃኑን የሚወክል፣ ዘመናትን የሚዋጅ ጽኑእ ብሔራዊ ትእምርት ለመቅረጽ ዕድል የሚሰጥ ይመስለኛል፡፡
የጤፍ ነገረ ኪን እና ፖለቲካም (the poetics and politics of teff) በቅኝት ከዚህ የሚለይ አይመስለኝም፡፡ ጤፍ በመጠን በአነስተኛነቱ “ዝነኛ” ነው፡፡ ለምሳሌ፣ አንድ የስንዴ ቅንጣት በአማካይ ከአንድ መቶ ሃምሳ የጤፍ ቅንጣቶች ጋራ እኩል እንደሆነ ይገመታል፡፡ ይህ ደግሞ “ከትውልድ ሥፍራው” አልፎ በዓለም ካሉ የእኽል ዝርያዎች በሙሉ በመጠን ትንሹ ያደርገዋል፡፡ በደስታ ተክለ ወልድ መዝገበ ቃላት ይህ የእኽል ዘር በተከታዩ መንገድ ተበይኖ እንመለከታለን፤ “ጤፍ፤ የታናሽ እኽል ስም፤ የሣር ዐይነት ሙርዬ የሚመስል፡፡ (ተረት)፤ ሳይቸግር ጤፍ ብድር” (19962፡ 675)፡፡[2] በዓለም ምግብ ድርጅት ገጽ ላይ ሰፍሮ እንደምናነበው፣ ጤፍ ከኢትዮጵያ ውጪ ባሉ አገራት፣ ለምሳሌ በደቡብ አፍሪካ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ከከብቶች ቀለብነት ባለፈ የአፈር መሸርሸርንና የውሃ ብክነትን ለመቀነስ ታስቦ የሚለማ “ተራ ሣር” ነበር፡፡[3] ተወዳጅ ነው በሚባልባት እናት አገሩም ቢሆን በመጠን ማነሱን ታክከው የሚቀርቡ ንጽጽሮች አጓጉልነት አላጣቸውም፡፡ ለአብነት፣ “ከመጤፍ አልቆጠረኝም” እና “ሰው ጤፉ” የሚሉ አገላለጾች በደረጃ ማነስን በገሀድ ያውጃሉ፡፡
ጤፍ በጄኔቲካዊ አወቃቀሩ እጅግ የተወሳሰበ፣ በጾታ ቅንብሩ የተደባለቀ (ፈናፍንት)፣ በምግብ ይዘቱ የበለጸገ የእኽል ዓይነት እንደሆነ የአዝርእት ባለሙያዎች ያስረዳሉ (ሰይፉ 1997)[4]፡፡ ሰይፉ ከተማ በመስኩ ላይ የተካሄዱ ምርምሮችን በከለሱበት ጽሑፋቸው እንደሚያስረዱን፣ የጤፍን የትውልድ ቦታ በእርግጠኝነት መናገር ቢከብድም፣ ጄኔቲካዊ ብዝኃነቱን በማጤን ኢትዮጵያ እናት ምድሩ ልትሆን እንደምትችል መገመት አስቸጋሪ አይሆንም፤ “[T]he genetic diversity for teff exists nowhere in the world except in Ethiopia, indicates that tef originated and was domesticated in Ethiopia” (12)፡፡ ጤፍ በዓለም አቀፍ ደረጃ እጅግ ጥንታዊ ከሚባሉ ጥቂት የእኽል ዘሮች መካከል አንዱ ነው፡፡ በዚህ የእኽል ዘር ላይ ከተካሄዱ ምርምሮች መካከል ብዙዎቹ፣ Nicolai Vavilovን (1951)[5] መሠረት በማድረግ፣ ቅድመ ክርስቶስ ከ4000–1000 በኢትዮጵያ ውስጥ እንደበቀለና ተስፋፍቶ እንደለመደ ይገምታሉ፡፡ እንደ ጤፉ ሁሉ፣ “ኢትዮጵያዊው” ማረሻ፣ ከዕድሜው ጥንትነት ባለፈ ልደትና ዕድገቱም እዚሁ መሆኑን የሚያመላክቱ ምርምሮች አሉ፤ ለምሳሌ፣ Hubert Cochet ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች በማረሻ ለ2000 ዓመታት እንዳረሱ ይጠቁማል (2011፡ 31)፡፡[6]
በኢትዮጵያ ውስጥ ከሦስት ሺህ በላይ ዘመናትን ያስቆጠረው፣ ከአገሪቱ ሕዝብ መካከል 70 ከመቶው በእንጀራ መልክ ይመገበዋል ተብሎ የሚገመተው ጤፍ (ታደሠ 2017፡ 50) በሦስቱ ዐበይት የሥነ ልሳን ቡድኖች ተቀራራቢ ስያሜም አለው፡፡ በአማርኛ “ጤፍ”፣ በኦሮምኛ “tafi” በትግሪኛ “ጣፍ”፡፡ በቀለም ስርጭትም ረገድ ወተት ከመሰለ ነጭ (ማኛ) አንስቶ እስከ ጥቁር ድረስ የሚዘልቁ አራትና አምስት ቀለማትን ያቅፋል (አዳም በሁሉም ቀለሞች የሚጫወት ሲሆን የበቀለ ምርጫ ጥቁሩ ነው)፡፡ እንዲህ ያለው የባሕርይ ውስብስብነት፣ የጾታ መንታነት፣ ኅብረ ቀለማዊነት ጤፍን–በአዳም ረታ ጥበበ ቃላት እና በበቀለ ዕይታዊ ጥበብ–ውስጥ ለብሔራዊ ትእምርትነት የተመቸ መባያ አድርጎታል፡፡ “ማረሻ” በበኩሉ ኢትዮጵያውያን የወል ምንትነታቸውን ከሚቀርጹባቸው ብሉይ ዕሤቶች መካከል አንደኛው ነው፡፡ የወልነቱን በዐበይቱ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ውስጥ ባለው የስያሜ ተወራራሽነት መረዳቱ አያሰቸግርም (የአማርኛው “ማረሻ”– በግእዝ “ማሕረስ”፣ በኦሮምኛ “maarashaa”፣ በትግርኛ “ማሕረሻ” የሚሉ አቻዎች አሉት)፡፡ ብሉይ ነው ስል አንድም፣ የዘፍጥረቱን ጥንታዊነት፤ አንድም፣ የጊዜ ጥልቀቱን ታክኮ የሚመሠረተውን ባህል ጽኑእነት ማመልከቴ ነው፡፡ በተፈጥሮው ቀጥ ያለው፣ የተሳለውና የሾለው ማረሻ፣ በበቀለ ትርኢቶች ውስጥ በከያኒው ፈቃድ፣ ፍላጎትና እጅ መዋቅሩ ተናግቶ፣ “ተፈጥሮው” ተዛብቶ ልክ እንደ ጤፍ ወደ ፈናፍንትነት ተቀይሯል፡፡ የበቀለ ማረሻዎች መዋቅር መናጋት የአድሏዊው የተባዕትነት ሥርዓት ፈርሶ በአዲስ ተምኔታዊ ሥርዓት የመተካቱ አምሳያ ነው፡፡ ከዚህ ሥርዓት ውስጥ ነው እንግዲህ ከያኒው አዳዲስና ነባር ዕሤቶች ተዳርተው የሚሰናኙበትን ብሔራዊ ትእምርት ለመፍጠር የሚታገለው፡፡[7]
ጤፍ እና ማረሻ ኢትዮጵያውያን ጥልቅ ከሆነ ጊዜ፣ የጋራ ታሪካቸውን፣ ርእዮታቸውንና ንጽረታቸውን የሚጠልቁባቸው፤ ሩቅ ከሚባል ትናንት የወል ልቡናቸውንና ምንትነታቸውን የሚያደሩባቸው “ቁሳዊ” ዕሤቶች ናቸው፡፡ ቤኔዲክት አንደርሰን፣ “It is the magic of nationalism to turn chance into destiny” (1983፡ 12)[8] እንዳለው ዕጣ ፈንታቸው ጭምር ተጠላልፎ የተሰናኘባቸው የወል ዕሤቶች፡፡ ማን ከዕጣው ማምለጥ ይቻለዋል? እንደሚታወቀው እንዲህ ያለ ዕሤት በጥልቅ ጊዜ እና በጽኑእ መሠረት ላይ የሚቆም አገር ለማነጽ ምቹ ዕድል ይፈጥራል፡፡ በእርግጥ አንድ ማኅበር በጽናት ይቆም ዘንድ ዕጣውን ከቋጠረበት ሩቅ ትናንት በተጨማሪ፣ በገነነ “የሕዝብ ማኅበራዊ ልቡና” ነገውን የሚዋጅበት የጋራ ስኬት እንደሚያስፈልገው አሌ አይባልም፡፡ ለዚህ ዓይነቱ ስኬት ጤፍ እንግዳ አይመስለኝም፡፡ ትናንት፣ ጤፍን ለሰው ልጅ ምግብነት በማዋል ረገድ ኢትዮጵያ ከዓለም ብቸኛ አገር ነበረች፡፡ ዛሬ፣ በተለይ በአውሮፓና በሰሜን አሜሪካ በሚኖሩ፣ እንጀራን መለያቸው ባደረጉ በ“ነባሬ ባዕድ”9 ኢትዮጵያውያን በሚተዳደሩ ምግብ ቤቶች አማካይነት ዝናን ያተረፈው ይህ የእኽል ዘር የኢትዮጵያን ድንበር ተሻግሯል፡፡ በጣዕሙ፣ በምግብ ይዘቱና ለጤና ባለው ጠቀሜታ ከተመጋቢው እኩል በሥነ ምግብ ተመራማሪዎች ዘንድ ተወዳጅ የሆነው ጤፍ በትልልቆቹ የዓለም የመገናኛ ብዙኋን ሳይቀር (ለምሳሌ፣ በBBC, VoA, The Washington Post, The Guardian, The New York Times, ወዘተ.) “the next ‘super grain’ of the World” የሚል መወድስ ወርዶለታል፡፡ ይህንን ዝና ተከትሎ ሊመጣ የሚችለው ማኅበራዊ ከፍታ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ–(as a national branding) ብሔራዊ ክብርና ኩራትን የመፍጠር አቅም አለው፡፡ የጤፍ ታሪካዊ፣ ባህላዊ እና ማኅበረ-ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው አንድም በመከባበር ላይ የተመሠረተ አንድነትን ለመፍጠር የሚያግዝ፤ አንድም በጎሣ፣ በሃይማኖት እና በቋንቋ ምክንያቶች የተፈረቀቀውን ብሔራዊ ልቡና (the national psyche) ለማከም የሚያስችል ዕድል እመስጠቱ ላይ ነው፡፡[10]
III
ትኩረታችንን ወደ ዛሬው ትርኢት እንመልስ፡፡ “ጤፍና ነጻነት”፡፡ ጤፍ የ“ኢትዮጵያ” እና “የኢትዮጵያዊነት” ብሔራዊ ትእምርት፤ ጋሻ በበኩሉ የነጻነት እና የአርበኝነት ማኅደር መሆኑን በመግቢያዬ አመልክቻለሁ፡፡ እንዲህ ያለው የጋሻ ትርጉም ህልው በሆነበት ባህል ውስጥ ጭምር ታውቆ የሚሠራበት ነው፡፡ በትርኢቱ ውስጥ ከቀረቡት ሥራዎች ብዙዎቹ ከጤፍ እና ከጋሻ ተራክቦ የተገኙ ናቸው፡፡ ይህ ማለት ግን ሁለቱ ጉዳዮች በሁሉም ትዕይንቶች ውስጥ እኩል ሥፍራ አላቸው ማለት አይደለም፤ በፍጹም፡፡ ጤፍ በሚናው ይልቃል፡፡ የጭብጥ ክትትል ከመፍጠር፣ የመተርጎሚያ ዐውድ ከመተለም ባለፍ ዝርው ህልውናም አለው፡፡ ጤፍ በቤት ውስጥ ቁስነት ተከስቷል፤ የግድግዳ ምርጊት ሆኖ ተገልጧል፤ ወዘተ፡፡ ጤፍ ታሪክ ነው፤ ምጣኔ ሀብት ነው፤ ፖለቲካ ነው፤ ርእዮተ ዓለም ነው፡፡ በጤፍ የሰው አካል ተገንብቷል፤ የሰው ገጽ ተነድፏል፡፡ ገጻተ ሰብኡ ከጤፍ መልኩንም ይዘቱንም ወርሰዋልና ወደ ጤፍነት ተለወጡ ማለትም እንችላለን፡፡ ከተጨባጭ ሁነቶችና ህልውናዎች ባለፈ ጤፍ ለልእለ አካላዊ ክስተቶች ማድሪያነት ውሎም እንመለከታለን፡፡ ለምሳሌ፣ “ጓዳና ግርግዳ” የሚል ርእስ በተሰጠው፣ በቀጫጭን ዘንጎችና በጥቁር ጤፍ ትግግዝ በተቀናበረ ግድግዳ ላይ (በጤፍ ቡኮ የተመረገ፣ ጋሻ ያዘለ ግድግዳ) ከያኒው ይሁነኝ ብሎ በተዋቸው ሽንትር ሽንቁሮች ውስጥ አሳልፈን የምናየው “የቤተ ክርስቲያን” ጨርቅ ልእለ ፍጥረት ህላዌ ከልደትና ሞት ጋራ የታተመበት ነው፡፡ በመሆኑም ጤፍ በትርኢቱ ውስጥ የነገረ ሰብእን ዕጣ የምናሰላበትን ስብርባሪ አፍታ ጭምር ይሰጠናል ማለት ነው፡፡
በትርኢቱ ውስጥ በጤፍ ከተገነቡ ምስሎች መካከል ገጸ ሰብእ[11] የተነደፈው በሁለት ተከታታይ ትዕይንቶች ውስጥ ብቻ ነው፤ በ“Gluten-free-dom I” እና በ“Gluten-free-dom II”፡፡ እነዚህ ትዕይንቶች “ተከታታይ” ብለን ብቻ የምናልፋቸው አይመስሉኝም፡፡ ይልቁንም እጅግ በተወሳሰበ ትእምርታዊነትና በተራቀቀ ዘይቤ የተከየኑ፣ ለፈርጀ ብዙ ንጽጽርና ትርጓሜ የተመቹ ወደረኛ ቅርጾች ናቸው፡፡ ኋለኛውን መነሻ እናድርግ፡፡ ጀርባ ለጀርባ እንጂ ፊት ለፊት የማይተያዩ፣ ትከሻ ለትከሻ ገጥመው ክብ የሰሩ የሰባት ነፍሰ ጡሮች ትዕይንት ነው፡፡ በዚህ ትዕይንት ውስጥ ሴቶቹ ክብነቱን ጠብቆ በጠባቡ በሚዞራቸው ቡላ ቀለም ያለው የአመድ ደለል ላይ ቆመዋል፡፡ ደለሉን ተከትሎ በክቡ የሰፈነው ነጭ አመድ ከሸማ የተሠራ ምንጣፍ፣ በዙሪያው የተኮለኮለው የከሰል ሰልፈኛ ደግሞ ጥቁር ጥለት ይመስላሉ፡፡ በሆዳቸው ፍሬ የያዙ ሰባት ሴቶች የተደራረቡ እጆቻቸውን ሐፍረታቸው ላይ ጣል እንዳደረጉ፣ እንጀራ የለበሰ ጋሻ አናታቸው ላይ እንደደፉ፣ በአክብሮት ይሁን በፍርሐት አልያም በሐፍረት አቀርቅረዋል፡፡
ሁለተኛው ትዕይንት የአንድ ሰው “ገድል” ነው፡፡ ይህንን ገድል እኔ “ገልና ገልቱ” ብዬ እጠራዋለሁ፡፡ (“ገል” የጋን ስባሪ፤ “ገልቱ” ያልሠለጠነ፣ በድንቁርና የተደፈነ፡፡) ዙሪያውን በተሰባበሩ ሸክላዎች የተከበበ፣ ከምድር ከፍ ብሎ የታነጸ፣ ባለ ስድስት ማዕዘን ቅርጽ ያለው ጡብ ገዝፎ ይታያል፡፡ ሙቀት ፍለጋ እጆቹን ወደ ፊት የዘረጋው ሰው እጡቡ አናት ላይ ባፍጢሙ እደፋው የአባቶቹ ጋሻ ላይ “ተመቻችቶ” ተቀምጦ “የደቀቁ የሸክላ ገሎችን በተመስጦ ይሞቃል”፡፡ ሁለቱ ትይዕንቶች የመከታተል ብቻ ሳይሆን እርስ በእርስ የመተረጓጎም ባሕርይም አላቸው፡፡ ይህንን ለማጤን እላይ በገለጻዎቹ ውስጥ የሰፈሩትን ወደረኛ ድርጊቶችና ሁነቶች ማነጻጸሩ ብቻ በቂ ይመስለኛል፡፡
ሴቶቹ በገዛ ፈቃዳቸው ፋታ ለማይሰጥ፣ ድካም ለበረታበት፣ ህመም ላለበት ኃላፊነት ራሳቸውን የሞሸሩ ይመስላሉ፡፡ አንድም የቁጥራቸው ሰባትነት የኃላፊነቱን ክብደት ያጸናል፡፡ ሰባት ቁጥር በትውፊት፣ በሃይማኖት፣ በኪነት፣ ወዘተ. ውስጥ ምልዐትን፣ ፍጹምነትን ለማመልከት ተመላልሶ የሚመጣ ነባር መባያ ነው፡፡ ፍጹምነቱና ሙሉነቱ የበረከትም የቅጣትም ሊሆን ቢችልም፡፡ አንድም ሴቶቹ የቆሙበት የአመድ ደለልም ሆነ አካላቸው ተገጣጥሞ የፈጠረው የቅርጽ ክብነት እላይ በቁጥር ጸና ያልነውን በድካምና በህመም የተሞላ ኃላፊነት ፍጹም ያደርገዋል፡፡ በክብነት ውስጥ መውጫ ቀዳዳ ይጠፋል፤ መነሻና መድረሻ ይታጣል፡፡ ለእረፍት የሚሆን ጥጋት አይሰጥም፡፡ በቀለ በምስሉ መግለጫ ላይ በገሀድ እንደሚጠቁመን ሰባቱ ሴቶች በዝርው ሰባቱን ቀናት ይወክላሉ፡፡ በዚህም ሰንበት ተገድፏል፤ የለመድነው የጊዜ መስፈሪያ ተሽሯል፡፡ ቀናቱ በሴቶቹ ድርጊት ተቃኝተው “ጊዜ” ከሰው ጋራ የሚለያይበት መስመር ደብዝዟል፡፡ መነሻ፣ ማጋመሻ፣ መዳረሻ የሚባሉ አንድም፣ የድርጊትና የሁነትና መሥፈሪያዎች፤ አንድም የጊዜ ዋቢዎች ሳስተዋል፡፡
እላይ በእንጥልጥል ወደተውነው ጉዳይ እንመለስ፤ “ገሎችን መሞቅ” ምን ማለት ነው? ከከያኒው ምስክርነት ባሻገር የወጣቱ የእጅ አዘረጋግ ሁኔታ በሙቀቱና በአካሉ መካከል በፈጠረው ሚዛን ሙቀትና ምቾት መኖራቸውን እንረዳለን፡፡ ግን እሳቱ ወዴት ነው? የሙቀቱ ምንጭስ ምንድ ነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች በአንድምታ የምንገልጠው እውነታ ካልሆነ በቀር፤ በቀጥታ የምናገኘው መልስ ያለ አይመስለኝም፡፡ በባለ ስድስቱ ማዕዘን ጡብ ዙሪያ በሰፊው የፈሰሱት የገል ስብርባሪዎች በኢትዮጵያውን የቆየ ታሪክ ውስጥ ቋሚ ሥፍራ ያላቸው፣ በሸክላ የተሠሩ አገረ ሰብአዊ ዕደ ጥበባት ናቸው፤ በየዓይነቱ –የጀበና፣ የምጣድ፣ የድስት፣ የጋን፣ የጣባ፣ የዕጣን ማጨሻ፣ ወዘተ. ስብርባሪዎች፡፡ ስብርባሪዎቹን በቅርበት ላጤነ ሰው ዕደ ጥበባቱ በእርጅና ምክንያት ከሰርክ ግብራቸው የተገለሉ አይመስሉም፡፡ ይልቁንም ከነወዛቸው ከነጉልበታቸው ያሉ፣ ከግብራቸው በግድ ተነቅለው የደቀቁ ነው የሚመስሉት፡፡ በሌላ ቋንቋ ሙቀቱ የሚመነጨው ከገሎቹ ትኩስነት ነው፡፡ ትኩስነት፤ አንድም፣ ከእሳት ምድጃ የሰበሰቡትን ሙቀት ይዞ ማቆየት ነው፡፡ ገልቱው ዕደ ጥበባቱን ከተሰየሙበት ምድጃ ላይ ነቅሎ –ቡናና ወጡን ደፍቶ፣ ዳቦና እንጀራውን ገልብጦ–ጀበናውን፣ ድስቱን፣ ገበር ምጣዱን፣ ምጣዱን አንክቶ፣ እንካቹን ሜዳ ላይ ዘርቶ ትኩስነታቸውን እየሞቀ ነው፡፡ አንድም በዘይቤ ተራ እንናገርና ትኩስነት አፍላነት ነው፡፡ የአገልግሎት ዘመን አለመጋመስ፡፡ ከብርታትና ጥንካሬ ጋራ መሆን፡፡ ጠላውን ደፍቶ፣ እርጎውን ገልብጦ፣ ወዘተ. ያደቀቃቸው የሸክላ ውጤቶች፡፡
በዚሁ ተጠየቅ ከተጓዝን የሴቶቹን አቋቋም በመመርመር በሰባት ቁጥር እና በክብ ቅርጽ ትግግዝ ጸና ያልነውን ህመም በተጨባጭ መመልከት እንችላለን፡፡ የሴቶቹ ፋታ የለሽነት ድርጊቶቹንና ሁነቶቹን በሙሉ ወደማያቋርጥ ሂደትነት ለውጧቸዋል፡፡ ይህንን ለማጤን–በተለመደው አገላለጽ–እንጀራ የጠመጠመ ጋሻ ከሰፈነበት የራስ ጸጉራቸው፣ በአመድ ደለል እስከተደበቀው የእግር ጥፍራቸው ድረስ መመልከቱ በቂ ነው፡፡ አመዱ እና እንጀራው ትይዩ ናቸው፤ አንዱ ምርት ሌላው ግርድ፡፡ ከአናት እንጀራው በተመረተ ቁጥር ከስር አዲስ አመድ ይወድቃል፡፡ አዲስ አመድ –ትኩሣቱን ያልጨረሰ አመድ፤ ረመጥ፡፡ ይህ ማለት ሴቶቹ ረመጥ ላይ ቆመዋል እንደማለት ነው፡፡
ቀደም አድርጌ ለማሳየት እንደሞከርኩት ሴቶቹ እንዲህ ያለውን በድካምና በህመም የተሞላ ኃላፊነት በፈቃዳቸው መርጠው ተቀብለዋል፡፡ በማሕፀኗ ሽል የያዘችን እናት በረመጥ እስከመድበን የሚያደርስ መስዋዕትነት ምን የሚሉት ኃላፊነት፣ እንዴት ያለ ዓላማና ተልእኮ ነው? የራስን ሰብእና የሚያደቅቅ፣ ህልውናን የሚያመነምን፣ ሕይወትን የሚያሰልል ተግባር ውስጥ በፈቃድ መሳተፍ ራስን ለከፋ ጉዳት ማጨት ይመስላል፡፡ የፈቃድ ጉዳት (self-destruction)፣ ከፍ ሲልም የፈቃድ ሞት ከዳግም ልደት ጋር የሚዛመዱበት እንዲህ ያለው አቀራረብ ሚታዊ አመሳሰል ነው፡፡ ይህን ዓይነቱን አመሳሰል በሚቶሎጂ ውስጥ በብሉየ መዋዕልና[12] ደንብ ከተቀረጹ ምስሎች (archetypal imageries) ጋራ አቆራኝተን መመልከት እንችላለን፡፡ በሆዳቸው ፍሬ የያዙ ሴቶች ትከሻ ለትከሻ ገጥመው ክብ መሥራታቸው፣ በሠሩት ክበብ ውስጥ ረመጥ ላይ መቆማቸው፣ በአመድ ደለል መያዛቸው፣ እንጀራ “ማብቀላቸው” በአንድ ግዜ ኦሮቡረስን (በክብነት) እና ፊኒክስን (በረመጥነት-አመድነት) አቃልጠን እንድናስብ ያደርገናል፡፡ ራሷን አቃጥላ ከትቢያዋ ላይ ነፍስ የምትዘራው ፊኒክስ (Phoenix) እና በክብ ቅርጽ ከጅራቱ አንስቶ ሙሉ አካሉን በልቶ በአዲስ ህልውና የሚከሰተው አሮቡሮስ (Ouroborus) “ሁለንተናዊ” ሊባሉ የሚችሉ የህመምና ድኅነት፣ የሞትና ልደት ትእምርቶች ናቸው፡፡ ባዶ እግራቸውን ረመጥ ላይ የቆሙ ሰባት እናቶች በቸልታ የተጎዳውን ነባር ምንትነት፤ በሆዷቸው የያዟቸው ሰባት ፍሬዎች ደግሞ እንደ አዲስ ይወለድ ዘንድ የሚጠበቀውን ርእይና ርእዮት ይወክላሉ፡፡ ከዚህ ትዕይንት ዓላማዎች መካከል አንዱና ምናልባትም ቀዳሚው ለዘመናት ለኖረው፣ ዳሩ ግን ቸል ለተባለው የእናቶች ህመምና ድካም–የላቀ ብሔራዊ ተግባር–ዕውቅና መስጠት ነው፡፡ ይህ ዕውቅና ልዕለ ሰብአዊ እና ልዕለ ታሪካዊ እንጂ ተርታና ሰርካዊ አይደለም፡፡ በሌላ ቋንቋ፣ ከያኒው ከፍ ባለ የአከያየን ስልትና ርእዮት እናቶችን ጥልቅ ጊዜ ውስጥ በመትከል ወደ ሚታዊ ተጋዳሊነት ቀይሯቸዋል፡፡ በምላሹም ከዚያው ጥልቀት ውስጥ በጽናት የሚቆም ብሔራዊ ትእምርት እና ብሔራዊ ምንትነት ለማስገር ሞክሯል፡፡
አንድም እናቶች ካለመኖር ህጽን መኖርን አስገኝተዋልና ለዚያም ኪናዊ ውዳሴ እንደ ማውረድ ሊቆጠር ይችላል፡፡ በአንዳንዶች ግምት “ጤፍ” የሚለው መጠሪያ “ጠፋ” ከሚለው ቃል የተገኘ ነው፤ ጠፋ፣ መኖር አቆመ፣ ህልውናው አበቃ እንደማለት፡፡ በሌላ ቋንቋ የዚህ የእህል ዘር የመጠን አነስተኛነት ከመኖር ይልቅ ላለመኖር ይቀርባል እንደማለትም ነው፡፡ የ“ጤፍ” የፍቺ ነቅኡ “ጠፋ” የሚለው ግስ ከሆነ፣ አንድም፣ ጤፍ የምንለው፣ በጣት የምንቆነጥረው ደቃቅ ነገር በተጨባጭ አለመኖርን ያስተማስላል (the representation of absence, the visibility of invisibilty) እንደማለት ነው፡፡ አንድም ዐውራውን የብሔራዊ ሚቶች መሻት–የመነሻዎች ሁሉ መነሻ የመሆንን፣ ከምንምነት ነቅእ የመፍለቅን መሻት–ይጠልፍልናል፡፡ ጤፍ አለመኖርን ከወከለ ከጤፍ የምንጠልቀው “ኢትዮጵያዊነት” ከእመ አበ አልቦ እንደተገኘ (creation ex nihilo, that is, creation from nothing) ይቆጠራል፡፡ በዘይቤ ተራ እንነጋገርና የኢትዮጵያ ገበሬ “አለመኖርን” ይዘራል፡፡ እናቶች ደግሞ ከአለመኖር ማሕጸን “እንጀራን” የመሰለ ግዙፍ ኑባሬ ያዋልዳሉ እንደማለት ነው፡፡ ከጤፍ አብራክ እንጀራ የመክፈሉን ጉዳይ፣ እናቶቹ በሆዳቸው ከያዙት ጽንስ መወለድ ጋራ አቆራኝቶ ማየት ይቻላል፤ ያ ጽንስ አንድም በነባርና በአዳዲስ እሴቶች ትብብር ይሸመናል ያልነው “ኢትዮጵያዊነት” (pan-Ethiopianism) ነው፡፡ የእንጀራው አናት ወጥቶ በጋሻ ቅርጽ መስፈኑ ደግሞ የልደቱ መፈጸም ማረጋገጫ ትእምርት ነው፡፡ ጋሻ የአርበኝነትና የነጻነት ትእምርት፤ ጤፍ ደግሞ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያዊነት ማደርያ ነው ካልን፣ በጋሻ መልክ የተከሰተው እንጀራ የዚህ ማረጋገጫ ሰንደቁ (the symbol of national imaginary) ይሆናል፡፡ አንድም በጋሻ ቅርጽ አናታቸውን የከበበው እንጀራ በሰማዕትነት እንዳገኙት የብርሃን አክሊል (halo or nimbus) ሊቆጠር ይችላል፡፡ እንዲህ ያለው ሐቲት ለኪነቱ በ“በብሉየ መዋዕልና” ደንብ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን አጥልቆ የሚተክልበትን ረቂቅ ዐውድ ይሰጠዋል፡፡
ኢትዮጵያውያን አንጀራን መመገብ የጀመሩበትን ጊዜ የሚያመለክት እርግጠኛ መረጃ የለም፡፡ ነገር ግን የእንጀራን መነሻ የሚጠቁሙ፣ ዘመኑን እስከ ቅድመ ክርስቶስ እስከ 100 ዓ.ዓ. የሚያደርሱ የቃል ተረኮች እንዳሉ ስትዋርትና አስናቀ ይናገራሉ (1962: 127)[13]፡፡ በእነዚህ ተረኮች ወስጥ እንጀራ ኢትዮጵያውያን በተቸገሩ ወቅት ከልእለ ፍጥረት ህላዌ የተሰጠ በረከት ተደርጎ ነው የሚቀርበው፡፡ (በበቀለ ኪነት ውስጥ ያንን ሚና ወደ ሚታዊ ህልውናነት የተሸጋገሩት እናቶች ወስደውታል):: ቀደም አድርገን የጠቀስነው የታደሠ ጥናት እንደሚያመላክተን (2017፣ 50) ከኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ 70 ከመቶ ያህሉ ጤፍን በእንጀራ መልክ ተመጋቢ ነው፡፡ ይህ ቁጥር የጤፍ እንጀራን ለብሔራዊ ምግብነት የሚያበቃው ይመስለኛል፡፡
ጋኖቹን[14] አንክቶ፣ ባፍጢሙ እደፋው ጋሻ ላይ ተቀምጦ ስብርባሪ ገሎች እየሞቀ በምቾት የሚመሰጠው ገልቱ በፈንታው ፍቺው የዚህ ተቃራኒ ነው የሚመስለው፡፡ በእኔ አረዳድ ትዕይንቱ የዘመናችን ክፉ አባዜ–አገር ለዘመናት ጸንታ የኖረችባቸውን የዕሤት ሥርዓቶች፣ የጋራ ታሪኮች፣ የወል ልቡናዎች የመቀናቀን አባዜ–በስላቅ የተነደፈበት ነው፡፡ ስላቁ የቤቱን ማገር እየመዘዘ በሚያነድድ፣ መሠረቱን እየቆረቆረ ቤቱን ራሱ ላይ በሚንድ ገልቱ ላይ ቢያርፍም፣ አገራዊ አደጋው የምር እና ቅርብ መሆኑን ትላልቅ ጋኖችን በማውደም አሳይቷል፡፡ አገር ጸናባቸው ያልናቸው ረቂቅ ዕሤቶች ወጣቱን በከበቡት ስብርባሪ ገሎች ገዝፈው ይታያሉ፡፡ “ጋን” ከአገረ ሰብእ ጥበብነቱ ባሻገር አገር አጽንተው ያቆዩትን ረቂቅ ዕሤቶች ለመወከል የሚያበቃ ሥነ ልሳናዊ እና ሥነ ፍቻዊ ባሕርይ አለው፡፡ በተለይም ቃሉ “ጋኖች” ተብሎ በብዙ ቁጥር ሲጠራ የፍቺው ስፋት ከማጀት እስከ አደባባይ ይዘልቃል፤ “ጋኖች፤ ትልልቆች ሰዎች ዋኖች ጨዎች ጎምቱዎች አባቶች ዐዛውንቶች፡፡ (ተረት)፤ ጋኖች ዐለቁና ምንቸቶች ጋን ኾኑ” (ደስታ ተክለ ወልድ፣ 280)፡፡ አንድም፣ ከማጀት እስከ ቤተ መንግሥት የተዘረጋ ፍቺ አለው፤ ከጠላ መጥመቂያ፣ ከጠጅ መጣያ ቁስነት እስከ ንጉሥ መጠሪያት የሚደርስ ፍቺ፤ የጃን ሆይ አቻ ሆኖ፣ “ጋን ሆይ ፤-ገናና ሆይ፤–ጃን ሆይ፡፡” (280) እያስባለ፡፡
እስካሁን ለማሳየት እንደሞከርኩት Gluten-free-dom “I” እና “II” በተወሳሰቡ ትእምርቶች እና በተራቀቁ እይታዊ ሜታፈሮች የተከየኑ ድንቅ ምስሎች ናቸው፡፡ በምስሎቹ መካከል የሚካሄደው ንጽጽር ከዚህም አልፎ ልሄድ ይችላል፡፡ እኛ ይህን በይደር ዘግተን ለመጣጥፉ እንደ ማሳረጊያ ወደሚያገለግሉ አንድ ሁለት ነጥቦች እንለፍ፡፡
IV
በትርኢቱ ውስጥ ከቀረቡት ሥራዎች ብዙዎቹ –ከፀሐይ እና ጎጆ (ከባህል እና ተፈጥሮ ) መስተጋብር ከተቀሰቀሱ የሰርክ ደፋ ቀናዎች (“አሁንና ቅድም” I፣ II፣ III)፣ የዘወትር ስሜቶች (“አዙረኝ አዛዙረኝ”) አንስቶ፤ ረቂቆቹ የወል ዕሤቶች፣ የጋራ ልቡናዎች እስከተከተቡባቸው ምስሎች (“ጓዳና ግድግዳ”፣ Gluten-free-dom “I” እና “II”) ድረስ ከጤፍ እና ከጋሻ ትእምርታዊ ተራክቦ የተገኙ ናቸው፡፡ እርግጥ ነው እንዲህ ካለው የትርኢት ጠቅላይ ፈለግ የሚሸሹ ጥቂት ሥራዎች አይጠፉም፡፡ ለዚህ ደግሞ፣ “የገደል ማሚቶ”፣ “ቆሜ ተቀምጬ” እና “አዲስ ጠላ በሰባራ አንኮላ” አብነት ይሆናሉ፡፡ “የገደል ማሚቶ” ለኀልዮ እምብዛም ያልተጨነቀ፣ ምናልባትም የሄደ ድምጽ ተመልሶ የሚመጣበት የቅርጾች ጨዋታ ነው፡፡ በ“አዲስ ጠላ በሰባራ አንኮላ” ውስጥ የጤፍና የጋሻን የተናጠልም ይሁን የወል ህልውና በገሀድ ፈልገን ስለማናገኝ ሥራው ከትርኢቱ አጠቃላይ መንፈስ ያፈነገጠ ይመስላል፡፡ ይሔ ግምት ግን ኪነቱን ከቀሪዎቹ ሥራዎች ጋራ አናብበን መተርጎም ስንጀምር በቀላሉ የሚፈርስ ነው፡፡ እንዲህ፣ እንደ “ጤፍና ነጻነት” ባለ አንድ ወጥ ርእስ በተሰጠው ከፍ ያለ ትርኢት ውስጥ ሥፍራ ያገኙ፣ በተቀራራቢ የጊዜ ክበብ ውስጥ የተከየኑ ሥራዎች በአመዛኙ ተነጥሎ ከሚከናወን ዝግ ምልከታ ይልቅ ለአጎራባች (co-textual) እና ለዐውዳዊ (contextual) ምርምር ይጋብዛሉ፡፡ ይህንን አጠቃላይ የነገረ ፍካሬ መርህ ከግምት ካስገባን፣ ከያኒው በምስሉ መግለጫ ላይ ባቀረበው ፍቺ ብቻ ረግተን የምንቆም አይመስለኝም፡፡ ይልቁንም በአንድምታ ተጨማሪ ትርጉም ለማከል እንጋበዛለን፡፡ በእኔ እምነት በትርኢቱ ውስጥ በአካል ጭምር የተጎራበቱት Gluten-free-dom “I” እና “አዲስ ጠላ በሰባራ አንኮላ” ከጤፍ እና ጋሻ መጉደል ባሻገር በገሎቻቸው ተሳስበው በመንፈስ ይሰምራሉ፤ በጭብጥ ይከታተላሉ፡፡ በትርጓሜም እንደሚከተለው ይተጋገዛሉ፡፡
በጥንታዊው የሒሳብ ማሰላሰያ፣ በአባከስ አምሳያ የተበጀው በአራት ማዕዘን የብረት ፍሬም የታጠረ ምስል፣ ብረቱ ላይ ሻጥ ሻጥ ተደርገው አግድም የተዘረጉ ወልጋዳ የእንጨት ዘንጎች፣ በዘንጎቹ ላይ የሚንሸራሸሩ በቅርጽና በመጠን የተዝረከረኩ ገሎች፤ የትርኢቱን አጠቃላይ መንፈስ የምንቃኝበትን የትችት አንጻር ጭምር ይሰጡናል፡፡ ገሎቹ በመሸራረፋቸው ቀድሞ የነበራቸውን የቅርጽና የመጠን አንድነት ማጣታቸው፤ ኢትዮጵያውያን የሃይማኖት፣ የቋንቋ፣ የአኗኗር ልዩነት ሳያግዳቸው ለዘመናት በወል የተጋሯቸውን ታሪኮች፣ ትዝታዎች፣ ሥነ ልቡናዎች፣ የዓለም ንጽረቶች አደጋ ላይ መውደቅ ያሳስባሉ፡፡ የከያኒው ትግል አንድም፣ አውዳሚነትና አጥፊነት የተጠናወተውን የዘመኑን “ገልቱ” መንፈስ መገሰጽ ነው፡፡ አንድም፣ ፈለጉን ብቻ እየተወ ቅኝቱን እያጣ፣ ከቅንብሩ እየወጣ፣ እየሰለለ እየመነመነ ያለውን የወል ዕሤትና ስሌት ቀርጾ ማስቀመጥ ነው፡፡
በ“ቆሜ ተቀምጬ” እናሳርግ፡፡ ይህ ሥራ በእርግጥ በጊዜ፣ በስሜት፣ በኀልዮ ከትርኢቱ አጠቃላይ መንፈስ አይገጥምም፡፡ ትዕይንቱ ተቀራራቢ የህልውናን ቅጥ (mode of existence) የሚጋሩ የአስር “ግለሰቦች” ሰልፍ ነው፡፡ በመቆምና በመቀመጥ መካከል የተተዉት አስሩ ገጻተ ሰብእ በአንድ በኩል በድርጊቶች፣ በሁነቶች፣ በስሜቶች፣ በአመለካከቶች፣ ወዘተ. መካከል የሚፈጠርን የድንበር መቃወስ ያመለክታሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በሁነቶችና በሁኔታዎች መካከል-ለምሳሌ፣ በኀልዮና በገቢር መካከል፣ በሕልምና በእውን መካከል፣ በኢንቃትና በንቃት መካከል–የሚከሰቱ ፈጣን፣ ዝንቅ እና እምቅ የሽግግር አፍታዎችን (liminal moments) ለዐይነ ኅሊና ይፈነጥቃሉ፡፡ በመሆኑም፣ ገጻተ ሰብኡ ከያኒው ሰርክ የማይገጥሙንን “የክት” አፍታዎች ቀልቦ የነደፈባቸው ዕይታዊ ዘይቤዎች ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ ይሄ በትርኢቱ ውስጥ ሰርጎ የገባ ሸላይ ጭብጥ ነው፡፡
[1] “መባያ” (motif) የሚለው ቃል በአንድ በኩል ለሚባለው፣ ለሚመሰለው ጉዳይ (object of representation)፤ በሌላ አንጻር ደግሞ ጉዳዩ ለሚባልበት ሁኔታ፣ ለሚመሰልበት መንገድ እና ለሚከየንበት መሣሪያ (manner, means and medium of representation) በመጠሪያነት እኩል ሊያገለግል ይችላል፡፡ አንድ ጉዳይ መባያ ይሆን ዘንድ በአንድ ዐውድ ውስጥ ተደጋግሞ ከመታየት፣ አልያም በተለያዩ ዐውዶች ውስጥ በቀረቡ ተከታታይ ኪናዊ ሥራዎች ውስጥ ተመላልሶ ከመምጣት በተጨማሪ ትእምርታዊ ሚና ሊኖረው ይገባል፡፡
[2] ደስታ ተክለ ወልድ:: ዐዲስ የአማርኛ መዝገበ ቃላት:: አዲስ አበባ፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት፣ 1962::
[3] “Traditional Crop of the Month,” FAO, https://www.fao.org/traditional-crops/teff/en/.
[4] Seyfu Ketema. Tef. Eragrostis Tef (Zucc.) Trotter. Promoting the Conservation and Use of Underutilized and Neglected Crops. Rome: Institute of Plant Genetics and Crop Plant Research, Gatersleben / International Plant Genetic Resources Institute-IPGRI, 1997.
[5] Nicolai Vavilov. The Origin, Variation, Immunity, and Breeding of Cultivated Plants, trans. K.S. Chester (New York: The Ronald Press, 1951).
[6] “A New Perspective on Animal Traction in Ethiopian Agriculture.” ITYOPIS, vol. 1, 2011, pp. (127-143).
[7] የበቀለን ማረሻዎች የአተረጓጎም ፈለግ በዝርዝር ለማግኘት ተከታዩን መጣጥፍ መመልከት ይቻላል፤ ቴዎድሮስ ገብሬ፤ “የነገሮች መቃ(የ)(ለ)ጥ፡ የበቀለ አሻራዎች”፡፡ በባሩድ እና ብርጉድ ውስጥ፣ ገጽ 6-17፡፡
[8] Benedict Anderson. Imagined Communities: Reflections on the Origin and Spread of Nationalism. London: Verso, 1983.
[9] ይህንን ሐረግ ከተሰማ ሀብተ ሚካኤል ነው የተዋስኩት፤ “ነባሬ ባዕድ”፤ ከልዩ ልዩ አገር እየ ፈለሱ የሚመጡና በንግድ፣ በጎሳነት፣ በዜግነት ዐብሮ የሚኖር ነባሬ ባዕድ ይባላል” (ገጽ 655)፤ ተሰማ ሀብተ ሚካኤል፡፡ ከሣቴ ብርሃን ተሰማ የአማርኛ መዝገበ ቃላት፡፡ አዲስ አበባ፣ ጎልደን አሳታሚ ፤ 2008 (1951)
[10] ይህ ጅምር ትእምርት በአዳም ረታ ልብ ወለዶች ውስጥ የእንጀራ አስተማስሎ ታክሎበት ወደ ላቀ ሚታዊ መባያነት ተሸጋግሯል፡፡ የአዳምን የጤፍ እና የእንጀራ አመሳሰል አሟልቶ ለመረዳት ተከታዩን መጣጥፍ መመልከት ይቻላል፡፡ Tewodros Gebre. “The Representation of Nation and National Identity in Modern Amharic Literature.” In Companion to African Literatures. Olakunle George (ed.). NJ: Wiley-Blackwell, 2021. 61-78.
[11] “ገጸ ሰብእ”ን በደፈናው የ“human figure” አቻ ነው፡፡ ሲበዛ “ገጻተ ሰብእ” ይሆናል (“human figures” እንደሚለው)፡፡ “ገጽ፤ በቁሙ፤ ፊት ግንባር፤ ዐይንና አፍንጫ አፍ ያሉበት፤ ካንገት በላይ እስከ ራስ ጠጉር ወደ ታችምእስከግር ጥፍር በስተፊት ያለው ክፍል” ማለት ነው፤ (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ:: መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ:: (አዲስ አበባ፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት፣ 1948፤ ገጽ 329):: ደስታ ተክለ ወልድ መጠሪያውን በሃይማኖት ዐውድ ወስነው ከመላእክት ጋር ብቻ አዝምደው (“ገጸ ሰብእ፤ ፊቱ የሰው የሚመስል መልአክ” እያሉ፤ ገጽ 299) ቢበይኑትም በፍቺ አስፋፍተን ልንገለገልበት እንችላለን፡፡
[12] “ብሉየ መዋዕልና፤ ቀዳማዊነት፤ ቅድምና፤ ዓለም ሳይፈጠር ዘመን ሳይቆጠር ቅድመ ዓለም መኖር” (ኪዳነ ወልድ 272)፡፡
[13] “Investigations of the Nature of Injera” በሚል ርእስ የዛሬ ስልሳ ዓመት አካባቢ የታተመው የስትዋርትና አስናቀ ጥናት፣ ቡሩክና ኃይሉ የተባሉ ባለሙያዎች፣ በ1958 (እ.አ.አ) ያዘጋጁትን ያልታተመ ሪፖርት መሠረት አድርጎ ነው “የእንጀራን አመጣጥ የሚያስረዳ አፈ ታሪክ አለ” የሚለን፡፡ ይህንን ሪፖርት ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ ዳሩ ግን እንጀራን በሚመለከት ለረጅም ዘመን ሲነገር የኖረ ሚታዊ ተረክ እንዳለ ዐውቃለሁ፡፡ በጥንት ዘመን ኢትዮጵያውያን ተርበው በተጨነቁ ጊዜ ንጉሣቸው የረሐቡ ምክንያት የሆነን ዘንዶ ጭንቅላት ፈልጦ ከውስጡ የጤፍ ፍሬ እንዳወጣ ይነገራል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ያንን ፍሬ እየዘሩ እንዳባዙ፣ ከዚያን ጊዜ አንስተው እንጀራ ጋግረው መብላት እንደጀመሩ ይተረካል፡፡
Stewart, Robert B. and Asnake Getachew. “Investigations of the Nature of Injera.” Economic Botany. 16. 2 (1962): 127-130.
[14] ቀደም አድርጌ እንዳሳየሁት ወጣቱ ሰባብሮ ከሚሞቃቸው አገረሰባዊ የሸክላ ሥራዎች መካከል በዚህ ትዕይንት ውስጥ የቀረ ያለ አይመስልም፡፡ ድስቱ፣ ምጣዱ፣ ጀበናው፣ ጣባው፣ መናጫው፣ ማጨሻው፣ እንስራው፣ ጋኑ፣ ወዘተ.፡፡ በዚህ የኪነት ዐውድ ውስጥ ጋን ከቀሪዎቹ የሸክላ ሥራዎች የላቀ ወካይነት አለው፡፡ አንደኛ፣ በትዕይንቱ ውስጥ ሰፊውን ሥፍራ የሚሸፍነው የጋን ስብርባሪ ነው፤ በቀለ ይህንን ትዕይንት ለመከየን ሁለት ትላልቅ ጋኖችን መስበር ነበረበት፡፡ ሁለተኛ፣ በባህሉ ውስጥ ጋን ከሸክላ ምርቶች ሁሉ “ታላቅ ዕቃ” ተደርጎ ይቆጠራል፡፡ ታላቅነት ከመጠን እና ከዕድሜ ያለፈ የጥበብ፣ የምግባር፣ የመንፈሳዊነት ብልጽግና አንድምታ አለው፡፡ በፍቺ ረገድ የ“ጋን” የቃል ሥር “ገነነ” ነው፡፡ ሦስተኛ፣ ጋን ለብዙዎቹ አገረ ሰብአዊ ዕደ ጥበባት እንግዳ በሆነ መልኩ ባለብዙ ሙያ ነው፤ ጠላ ይጠመቅበታል፤ ጠጅ ይጣልበታል፤ ሊጥ ይቦካበታል፤ ሸማ ይከተትበታል (ደስታ 280)፡፡ አራተኛ፣ ጋን ከለመድነው ፍቺ የሚልቁ አንድምታዎችን ለማዝመር የሚያስችል መጠሪያም ነው፡፡ ይህ ባሕርይው ቃሉን፣ አንድም ለመልከ ብዙ ፍካሬ እንዲስማማ፤ አንድም ለሚስፋፋ ፍቺ እንዲመች ያደርገዋል፡፡