ረዳት ፕሮፌሰር ቻላቸው ፈረጅ

ተወዳጅ ሚድያ እና ኮምዩኒኬሽን ፣ መዝገበ-አእምሮ ( የአማርኛ ኢንሳይክሎፒዲያ ) ፕሮጀክቱ ለአገር የሠሩ ሰዎችን ታሪክ እየሰነደ እንደሆነ ይታወቃል። ይህ ታሪክ በዲጂታል ሚድያዎች ፣በመፅሀፍ፣በድምፅ ትረካና በሌሎችም መንገዶች እየቀረበ እንደሆነ ይታወቃል።በተለይ ጉግል ላይ ታሪካቸው ሲፈለግ የማይገኝ ሰዎች አሁን የሙያ አበርክቷቸው በቀላሉ ኢንተርኔት ላይ በግልፅ ተቀምጦ ይገኛል። ባለፉት 4 ዓመት ከ 5 ወር ጊዜ ውስጥ የ423 ሰዎችን የሕይወትና የሥራ ታሪክ ለመሰነድ የቻልን ሲሆን 600 ገፅ ባላቸው ሁለት የተለያዩ መፅሐፎች ላይም ታሪኮቹ ዘመን ተሻጋሪ ሆነው እንዲቀመጡ አድርገናል።

ከእነዚህ ውስጥ የሚድያ ሰዎችና የቴአትር ባለሙያዎች ይገኙበታል። አጠቃላይ 74 ከፍተኛ የሚድያ አመራሮች፣ 50 በላይ የፊልምና የቴአትር ባለሙያዎች ፣ሚኒስትሮች ፣ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የግል ሚድያ መሥራቾች፣ዋና አዘጋጆች እና መካከለኛ አመራሮች ተካተዋል። 35 ያህሉ በዋና ሥራ አስፈጻሚ ደረጃ ያሉ ሲሆን የሁሉም ታሪክ በተሟላ ደረጃ ለመሰነድ ተችሏል። የእነዚህን አመራሮች እና የሚድያ ሰዎች ታሪክ ሰንዶ ለአንባቢ ተደራሽ ማድረግ ፈታኝ ቢሆንም አሳክተነዋል። በዚህ ተግባራችንም ተጠናክረን እንቀጥላለን።

በዚህ ፅሑፍ የሙያ ታሪኩ የሚሰነድለት የቴአትር ባለሙያ ረዳት ፕሮፌሰር ቻላቸው ፈረጅ ነው። የቴአትር መምህር የሆነው ቻላቸው በብርቱ ባለሙያነቱ ይመሰከርለታል። ሙያውን ስለመውደዱ እና ስለማክበሩ ይነገርለታል። የመዝገበ አእምሮ የጥናት ቡድንም ይህን የሚያውቁትን በመጠየቅ አረጋግጧል ። ስለሆነም ታሪኩ ለትውልድ መቀመጥ አለበት ብለን እምነት በማሳደራችን የባለታሪኩን ይሁንታ እና ማረጋገጫ በማግኘት የሙያ ታሪኩን አቅርበነዋል። ዕዝራ እጅጉ ታሪኩን እንደሚከተለው ሰንዶታል።

📷 ቻላቸው ፈረጅ ነሐሴ 14 1976 ዓ.ም በምዕራብ ጎጃም ዞን፣ ሜጫ ወረዳ፣ መርዓዊ ከተማ ተወለደ። ዛሬ ለትያትር ያለው ፍልስፍና ገና በልጅነት ለቃል፣ ለእንቅስቃሴ፣ ለከበሮ ድምፅ፣ ለዘፈን፣ ለጭፈራ፣ እና ለተረት ነገራ ከነበረው መሰጠት ዛሬም ድረስ ካልተለወጠው ዝንባሌው እና ጽኑ ፍቅሩ ይነሣል። ለእርሱ ትያትር ከመድረክ ጋር ብቻ ታስሮ ቀሪ ጥበብ አይደለም። ይልቁንም ትያትር ማኅበረሰብ ትዝታውን፣ ጥያቄውን፣ ሞት ሽረቱን እና የነገ ምናቡን ከእራሱ ጋር የሚያወጋበት ሕያው ቋንቋ ነው።
ቻላቸው በመጀመሪያ በጎንደር መምህራን ኮሌጅ በቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ያገኘው ሙያዊ ትምህርት ቃልን እንደ ክቡር ሀብትና እሴት የሚወስድ ጠቢብ እንዲሆን ምክንያት ሆኖታል። ከዚህም የተነሣ የተጻፈ ሆነ የሚነገር ቃል ለግብረ-ገብ እና ለባሕል የሚወሰድ ኃላፊነት ነው ሲል መቀበልን ጀመረ። ይህ መሰረትም ንግግር ኃላፊነትን ተሸካሚ እንዲሆነና፣ ትያትርም እንደ ግብረ ገባዊ ጥበብ አስኳሉ ግለሰብን ከማኅበረሰብ እና ካለፈ ትውስታ የሚያስተሳስር ገመድ ነው የሚለውን የሕይወት ሙሉ እምነቱን እንዲመሰርት አስችሎታል።

በኋላ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በትያትርና ፊልም ጥበብ የቀሰመው ትምህርት ደግሞ ይህን እምነቱን በአካዳሚክ እውቀት አጽንቶ እንዲያስር ረዳው። በከፍተኛ ማዕረግ ያጠናቀቀው የመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርት ሲጠናቀቅ ሥልጡን ተግባሪ ብቻ ሳይሆን ትያትርን የእውቀት ሥርዐት ነው ብሎ የሚመረምር አሳቢ/ተፈላሳፊ ባለሞያ አደረገው። ለጥቆ በአካዲሚው ጉዞ መስመር በ2ኛ ዲግሪ ያገኘው ብዝኀ-ሚዲያ ትያትር ትምህርት ድምፅ፣ ምስል፣ ብርሃን፣ እንቅስቃሴ፣ ሪቹዋል፣ እና ቴክኖሎጂ ባንድ ገጥመው ነጠላ ገላጭ የመተረኪያ ቋንቋ ቢሆኑም በሕብረት ተሰናስለው በአንድ ማዕድ በተግባር ማቅረብን አወቀበት። በአሁኑ ወቅት እጩ የዶክትሬት ተማሪ መሆኑ ትያትርን እንደ ባሕል፣ ማሕበረሰባዊ እና ፍልስፍናዊ ልምምድ ጥናት ለቀጠለው ፍለጋው ምስክር ነው።

ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ ቻላቸው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትያትርና ፊልም ጥበባት ትምህርት ቤት ከረዳት ምሩቅነት ተነስቶ፤ ዛሬ በረዳት ፕሮፌሰርነት እያገለገለ ይገኛል። ማንነቱ ግን ከደረሰበት ትምህርት ደረጃ ያለፈ ነው። ምክንያቱም ከሚያስተምርበት ክፍል ተሻግሮ ወደ ማሳያ ስፍራዎች፣ ጎዳና፣ ስታዲየም፣ አደባባዮች እና ብሔራዊ ክብረ በዓላት ላይ ሳይቀር ዘልቀው የሚያልፉ ተግባሪ ምሁር ነው። ለእርሱ ተማሪ የሚማረው የትያትር ቴክኒክና ክህሎት ብቻ ሳይሆን ከማኅበረሰብ ጋር በንቃት፣ በጀግንነት፣ እና በምናብ ለማቆም የሚተጋ ኃለፊነትን ጭምር እንዲሸከም ነው።

✍️ጥበባዊ ዘዴ እና ፍልስፍናዊ ርዕይ

የቻላቸው ጥበባዊ ዘዴ እርስ በእርሳቸው በሚሻመኑ ሦስት መርኅዎች ውስጥ የተመሰረተ ነው። እነርሱም የጋራ ትውስታ፣ በተምሳሌት አጥርቶ ማየት፣ እና ከሕዝብ ጋር መኖር ወይም መወገን ናቸው። ትያትር ሁልጊዜ የግድ ወደ ሕዝብ መሄድ አለበት ብሎም ያምናል። ሲሄድም ከላይ ሆኖ ለማዘዝ ሳይሆን ይልቁም ከውስጥ እና ከልብ ለመነጋገር ታሳቢ በማድረግ እንጂ። ሥራዎቹ በአብዛኛው በአመልካችና ተመልካች መካከል የሚኖርን ድንበር ይቀላቅላሉ። ይህም ተመልችን የራሱ ጉዳይ እማኝ እና ተሳታፊ ያደርጋል።

የትያትር ተለምዶአዊ ፎርሙላዎችን በመተው በተለይ የአመልካችና ተመልካችን ግንኙነት መልሶ ለመበየን ያልተለመዱ ፈጠራዊ የአቀራረብ ዓይነቶች ላይ ሙከራዊ ልምምድ ያደርጋል። በተለምዶ ውርስ የሆኑ የትያትር ሕግጋትን ሆን ብሎ በመስበር፣ ትርኢታዊ አቀራረቦችን መልሶ በመቅረጽ እና ተሻጋሪ እንቅስቃሴ እና ቅርርቦችን በመፍጠር ከዝንጉ ተመልካች ይልቅ በሥራዎቹ ንቁ፣ ለሂስ ዝግጁ የሆነን ተመልካች እንዲከሰት ይጥራል። እራሱን ተግባሪ እና ዘመነኛ የትርኢት ንድፈ ሐሳብ ተላሚ ቦታ ላይ ማስቀመጥ አንዲያስችለው አማራጭ የትወና ድርብ ቴክኒኮችን እና ሁሌ አንድ ዓይነት ያልሆነ ያቀራረብ ስልቶችን፣ እና ያልተቋረጠ አዳዲስ የሙከራ ሥነ ውበታዊ የእድል አጋጣሚዎችን ጥቅም ላይ ያውላል።

በዚህ ርዕይ ላይ በመመስረት በዓለም አቀፍ ደረጃ ዘመነኛ በሆነው፤ በሀገር አውድ ደረጃ ግን ገና እንግዳ በሆነው የብዝኀ ሚዲያ ትርኢት አቅርቦት ረገድ ቻላቸው ያለው ተሳትፎ ከንድፈ ሐሳባዊ አቅም ከፍ ብሎ የተሻገረ ዘላቂ ተግባራዊ ያጠቃቀም ፋይዳን ተገንዝቦ እየተገበረ የሚገኝ ባለሙያ ነው። የእርሱ አቀራረብ ትርኢትን የተሰባጠሩ መግለጫ መድረኮች ማለትም ትያትር፣ ራዲዮ፥ ቴሌቪዥን፣ ፊልም፣ ዳንስ፣ ጋዜጠኝነት፣ መጽሔቶች፣ ሙዚቃ፣ ስዕል፣ ፎቶግራፍ እና ሌሎች የእይታና የድምፅ ሚዲያ በተቀናጀ እና ስሙር ጥበባዊ ሲነርጂ የሚገናኙበትን መሰረታዊ ምሰሶ ይጠቀማል። ይህ ስምረት ሀቅ ደረቅ መረጃ ሳይሆን በስሜት ሕዋሳት የሚዳሰስ እውነት የሚኖር ሲሆን በአስተውሎት ንቁ አና በመተርጎምም የሚያውቅ ተመልካች እንዲኖር አጥብቆ ይሰራል።

የብዝኀ ሚዲያ አጠቃቀም የትርኢትን መኖር አስፈላጊነት የማጉላት አቅሙ ባላደገበት የክዋኔ ጥበባት ሀገር የቻላቸው ሥራዎች ፈር ቀዳጅ ጥረቶች ሆነው ይታያሉ። ይህ አቀራረብ ከዘመነኛ አስፈላጊነት ባሻገር ተዝናኖትን ከተጨባጭ ማኅበረሰባዊ እውነታዎች ጋር በማጋባት የተግባቦት ኃይልና ሕዝባዊ ዋጋ ያላቸውን ጥበባዊ ሥራዎች ለመሥራት ያስችላል። በመሰባጠር ውስጥ ያለ አንድነትን መሰረት በማድረግ እና በተባዥነት ውስጥ ያለን ሥነ ውበታዊ ጸጋን በማብራት የቻላቸው ልምምድ የጥበብን ታላቅ ማሕበራዊ ኃላፊነት የሚያስረዳ ነው። ረ/ፕሮፌሰር ቻላቸው ይህን ግንዛቤ በትክክለኛ ዳኝነት በመተግበር ጥበባዊ ቅርጽ የጋራ ንቃተ-ሕሊናን ለመግለጽ እና መልሶ ለመቅረጽ ሲል ይተገብራል።

በፍልስፍና ደረጃ የእርሱ ትያትር ትርኢትን ለትርኢት ብቻ የሚለውን ሐሳብ ይገዳደራል። በታላላቅ ስታዲየሞች እንኳን የትርኢቶች ልኬት ትርጉም አላቸው። ሥፍራዎች ትርክት ይሆናሉ፣ አካላት መዛግብት ይሆናሉ፣ ሙዚቃ በጉዞ ላይ ያለ ታሪክ ነጋሪ ይሆናል። ሥራዎቹ ዘላቂ ጥያቄዎችን ያነሳሉ። አብሮ መሆን ማለት ምንድነው? ያለፍን የመርሳት ዋጋው ስንት ነው? ሀገር ከእነራሷ ጋር በታማኝነት እንዴት ታወጋ ይሆን? የመሳሰሉ አቀንቅኖትን ያጋባሉ።

✍️ዋና ዋና ሥራዎቹ

  • አባይ እና ወርሱ
  • ጎህ ሲቀድ
  • የሩቅ ቀን መንገደኛ
  • ሐረር ኢትዮጵያ
  • ሼክ አባድር
  • ሉሴ
  • ሳንወድቅ እንወቅ
  • አንዱ ለሁሉም ሁሉም ለአንዱ
  • የጽናት ልጆች
  • የአራቱ መጽሐፍት ወግ
  • የጀግኖች መዝገብ
  • ቃልን ያከበረ በቃል የከበረ
  • ሰባ አምስት ዓመታት የእውቀት ጉዞ
  • አድዋ ሕያው ተጋድሎ ሕያው ድል
  • ዴሞ ምጥ

ከእነዚህ ሥራዎች ጎን ለጎን ቻላቸው ታላላቅ ብሔራዊና ሕዝባዊ እሳቤ ያላቸው የመድረክና የስታዲየም ትርኢቶችን በማዘጋጀትና በመፍጠር ይታወቃል። ይህም “ሐገር፣ ሰውና ስፖርት” ፣ ሐረር ኢትዯጵያ፣ ሐረር አባድር፣ ሉሲ፣ ወዘተ ይካትታል። እንዚህ ሥራዎች በጥበብና በሀገር መስተጋብር ውስጥ የሚያርፉ ሲሆን ቲያትር የጋራ ሕዝባዊ ክብረ በዓል ጥንታዊ አካልነቱን ወይም ጠባዩን ለመመለስ በሐገር ደረጃ በመስራቱ በታሪክ ሊወሳላት የሚገባ ጉዳይ ነው።

✍️ትያትር እንደ ሕዝባዊ ኃላፊነት

ከመድረክ ባሻገር ቻላቸው በርካታ ማኅበራዊ ጉዳዮችን አንስተው ንቃትን በሚፈጥሩ እና ሕዝባዊ ውይይቶችን በሚፈጥሩ አሳታፊና ብዝኀ ሚዲያ ቴያትሮች ላይ በሰፊው ሠርቷል። ከተለያዩ የመንግስት እና መንግስትታዊ ያለሆኑ ተቋማት ጋር እንዲሁም ከባሕል ቢሮዎች ጋር የሠራቸው ሥራዎቹ ጥበብ ቅኔያዊ ለዛና ጥልቀቱን ሳያጣ እውነተኛ ማኅበራዊ ርዕሰ ጉደዳዮችን መነሳት አለበት ለሚለው የጸና እምነቱ አብነቶች ናቸው።
እንደ ጥናት እና ምርምር ባለሞያ በኢትዯጵያ ትያትር እና ተጽእኖአቸው ከፍተኛ በሆኑ አንጋፋ ባለሞያዎች ላይ የጻፋቸው ሥራዎች ባለፉት መሪ ጥበበኞች እና በአሁኑ ፍልሰፋ መካከል ቀጣይነትን የሚያበራቱ ናቸው። በምሁራዊነት ውስጥም ቢሆን ቻላቸው ልምዱ በተግባራዊነት ውስጥ የተቃኘ በመሆኑ ለእርሱ ጥናት ትውስታ ትንታኔ ዳግም አክብሮት የሚያሰጡት ናቸው።

✍️ሕያው ልምምድ

ቻላቸው ፈረጅ ድምዳሜን የሚሰጥ ጠቢብ አይደለም፣ ሙግቶቸን ያነሳሳል እንጂ። ሥራው የጋራ ንቃትን ይፈጥራሉ እንጂ የማብቂያ መልስን አያሳድዱም። በኢትዮጵያዊ የባሕል እውቀት ሥሩን ተክሎ ለዓለም አቀፋዊ ምክክር በሩን ከፍቶ የእርሱ ቴያትር ጥበብ ለሕዝብ፣ ለሀገር ግንባታ ጥረቶች፣ ለታሪክ፣ እና ለከርሞ ሀገራዊ ህልም የግድ ተጠሪ መሆን እንዳለበት አብሳሪዎች ናቸው።
የረ/ፕሮፌሰር ቻላቸው ሥራ መድረክ ላይ ቢከወኑም ነገር ግን ወደ መማሪያ ክፍሎች፣ ወደ ማኅበረሰብ፣ ወደ ሕዝብ ሁሉም እራሱን እየተረከ ለኖረው የ ኅብረተሰብ የጋራ ምናብ ከሳቾች ናቸው።

 ✍️ ስለ  ረዳት ፕሮፌሰር ቻላቸው  ምስክርነት 

የባህልና ኪነጥበብ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ረዳት ፕሮፌሰር ነቢዩ ባዬ ቻላቸውን በኢትዮጵያ የቴአትር ጥበብ አድማስ የተወለደ ወጣት ምሁር ሲሉ ይገልፁታል።

አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ አመቱን እጅግ በደመቀ እና ትርጉም ባለው መንገድ ሲያከብር በዚህ አከባበር ወቅት ጥበብ ከፍ ያለ ሥፍራ ወሰዳ ዩኒቨርሲቲያችንን ገልጣለች። በዚህ ታሪካዊ ክንዋኔ እንደ ትልቅ የጥበብ ሰው የተወለደን አንድ ወጣት መምህር፣ አንድ ብርቱ ሰው ማመስገን የተገባ ነው። ያም ሰው ቻላቸው ፈረጅ ነው” ሚኒስትር ዴኤታው ምስክርነት መስጠታቸውን ይቀጥላሉ።

“…..ቻሌ የዩኒቨርሲቲው ቴአትር እና ፊልም ጥበባት ክፍል ወጣት መምህር ነው። ትምህርት ክፍሉን የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቶ ሲመረቅ መምህሩ ሆኜ ችሎታውን እና ታታሪነቱን ለሦስት ዓመታት በሚገባ አውቃለሁ። መምህር ሆኖ ከተቀላቀለበት ጊዜ አንስቶም በባልደረባነት እጅግ የሚያኮራ ሰብዕናውን እና ጥረቱን ለማወቅ ችያለሁ። ለመምህራኑ እና ባልደረቦቹ በተለይም ለተማሪዎቹ ያለውን ፍቅር እና ክብር ለቴአትር ጥበብም ያለውን ቀናዒነት እና ትጋት ጠንቅቄ አውቃለሁ። ማስተርስ ሲማርም በመምህርነቴ እየበሰለና ከኢትዮጵያ የቴአትር ጥበብ ግምባር ቀደም ባለተስፋዎች አንዱ እየሆነ ሲበረታ ማስተዋለሰ ችያለሁ። ቅንነት፣ አስተዋይነት፣ ትህትና፣ ታዛዥነት እና ተባባሪነት፣ ጠንካራ ሥራ፣ ሀገር ወዳድነት፣ የዘወትር ተማሪነት፣ ታታሪነት፣ ታታሪነት ታታሪነት ይኼን ልጅ ገልጠውልን ወደን አክብረነው ኖርን። የዩኒቨርሲቲው ሰባ አምስተኛ አመቱን ሲያከብር እኛ የምናውቀው ባለተስፋ ወጣት የዩኒቨርሲቲውን የሰባ አምስት አመት ጉዞ በጥበብ ጉዞ ያሳየውን ሄሪቴጅ ወክ ሥራ በመምራት ለሁሉ ተገለጠ። በዘመናዊ አቀራረቡ ለሀገራችን አዲስ የሆነ የጉዞ ቴአትር ከአራት ኪሎ ፕላዛ እስከ ስድስት ኪሎ ዋናው ግቢ ድንቅ አድርጎ መራ።

ከ1943 የዩኒቨርሲቲው ምሥረታ ጀምሮ ያለፈበትን ሂደት ከሀገራችን የታሪክ ሂደት ጋር በማቆራኘት በእግር ጉዞ ቴአትር አቀረበው። ታዋቂዎቹ የዩኒቨርሲቲ ኅብረ ዝማሬዎች፣ ጥልቅ የትረካ ትወናዎች፣ የየዘመኑ ገላጭ አልባሳት፣ ገፀቅብ፣ ቁሳቁስ(መፈክሮች እና ስዕሎችን ጨምሮ) የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን፣ የደርግን፣ የኢህአዴግን አልፎም ያለንበትን እና የደረስንበትን የዩኒቨርሲቲ ራስ ገዝ ጅማሮ በአስደማሚ መንገድ አቅርቦታል። ወደ ሁለት መቶ የሚጠጉ ተዋንያንን፣ ሙዚቀኞችን፣ የሰርከስ ትርኢት አቅራቢዎችን፣ ሰአሊያንን ድርሰት ፅፎ፣ በተለያየ ቡድን ዳይሬክት አድርጎ፣ የመጨረሻውን ትርኢት ከመጀመሪያ እስከ መደምደሚያው መርቶ የጥበብ ታሪክ ሰርቶልናል። በሰራው ታሪክ በዩኒቨርሲቲው በጥበብ ተወልዶልናል። እንኳን ደስ አለህ፣ በርታ እንለዋለን። ” በማለት ስለ ቻላቸው ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *